Saturday, July 07, 2018

በደም የተሳሰረውን ግንኙነት የማስቀጠል እርምጃው ይጠናከር

(July 07, (ርዕሰ አንቀፅ))--የኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዝቦች የጋራ ባህል፣ ቋንቋ፣ ሃይማኖትና እሴቶችን የሚጋሩና በብዙ መልኩ የሚተሳሰሩ ናቸው፡፡ ኤርትራ በሕዝበ ውሳኔ በ1985 ዓ.ም ከኢትዮጵያ በመገንጠል ራሷን የቻለች አገር ብትሆንም፤ በአገራቱ መካከል በድንበር ጉዳይ በተፈጠረ አለመግባባት በ1991 ዓ.ም ወደ ጦርነት ተገብቷል፡፡ ይህም ከ70ሺ በላይ ሰዎችን ለሞት፣ በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩትን ለከባድና ቀላል የአካል ጉዳት፣ በብዙ ሚሊዮን ብር የሚቆጠር የሀብት ውድመትን አስከትሎ አልፏል፡፡

ጦርነቱን ተከትሎ ችግሩን በሕጋዊ መንገድ ለመፍታት ጉዳዩ በገለልተኛ አካል እንዲታይና እንዲወሰን ተደረገ፡፡ በዚህም መሠረት የኢትዮጵያና የኤርትራ የይዞታ ይገባኛል ጥያቄ በአልጀርስ ስምምነትና በድንበር ኮሚሽን ውሳኔ ተደመደመ፡፡ ውሳኔውን ተከትሎ ኢትዮጵያ በአፈፃፀሙ ዙሪያ ከኤርትራ መንግሥት ጋር መደራደር እንደምትፈልግ በተደጋጋሚ ሙከራ ብታደርግም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ የዚህ ውጤትም በቀጣናው ለ18 ዓመታት ያህል ሠላምም ጦርነትም የሌለበት ሁኔታ ከመፍጠሩም በላይ፤ አካባቢው ከልማትም ርቆ እንዲቆይ አድርጓል፡፡

በድንበር አካባቢ የሚገኙ ነዋሪዎችም በ«ሞት አልባው ጦርነት» ቀጣና በስጋት ውስጥ ሆነው ኑሮን ለመግፋት ተገደዋል፡፡ የኢትዮጵያ የፀጥታ አካላትና ወታደሮችም ለረጅም ዓመት በተጠንቀቅ ቆመው ዳር ድንበራቸውን ሲጠብቁ ከርመዋል፡፡ ለዚህ ሥራም መንግሥት የተለያዩ የሎጅስቲክስ አቅርቦቶችን በማሟላት ለከፍተኛ ውጪ መዳረጉም አይካድም፡፡

አሁን ታዲያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ኢትዮጵያ የአልጀርሱን ስምምነትና የድንበር ኮሚሽኑን ውሳኔ ተቀብላ ለመተግበር የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ መወሰኑን በመግለፅ ለኤርትራ መንግሥት ያቀረቡት የሠላም ጥሪ በኤርትራ አቻቸው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ በኩል በጎ ምላሽ አግኝቷል፡፡ የኤርትራ ልዑካን የሆኑት የፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ አማካሪና የፖለቲካ ጉዳዮች ኃላፊ አቶ የማነ ገብረአብ እና የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ኦስማን ሳለህ ትናንት አዲስ አበባ ገብተዋል፡፡ ልዑካኑም ከመንግሥት ጋር ገንቢ ውይይት ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የኤርትራ መንግሥት የሠላም ጥሪውን ተቀብሎ ችግሮችን በሠላማዊ መንገድ በመፍታት አብሮ ለመጓዝ መወሰኑ የሚደነቅም የሚመሰገንም እርምጃ ነው፡፡ የቆየውን ቁርሾ በሠለጠነ መንገድ በክብ ጠረጴዛ ዙሪያ ተወያይቶና ተመካክሮ መፍትሔ ለማበጀበት መዘጋጀቱና ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩ ይበል ያሰኛል፡፡ ለሁለቱ አገራት ሠላማዊና የጋራ ጥቅምን መሠረት ላደረገ ግንኙነት ትልቅ መደላድል የሚጥል ነው፡፡ ተራርቀውና ተነፋፍቀው ለቆዩ ሕዝቦችም ትልቅ ብስራት ይሆናል፡፡ የሠላም ጥሪው በተግባራዊ እንቅስቃሴ መታጀቡ የሁለቱ አገራት ቀጣይ ጉዞ ብሩህ እንዲሆን ያግዛል፡፡

ሁለቱ አገራት የወሰዱት እርምጃ በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል ተፈጥሮ የቆየውን አለመግባባት በመፍታት ዘላቂ ሠላም እንዲፈጠር ያደርጋል፡፡ በደም በተሳሰሩት ወንድማማች ሕዝቦች መካከል ተቋርጦ የነበረው ወዳጅነት በአዲስ ምዕራፍ እንዲጀመር ይረዳል፡፡ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱን በማጠናከር ማህበራዊ ትስስሩን ለማጎልበት ያግዛል፡፡ ከኤርትራ ወደ ኢትዮጵያ የሚደረገውን ስደት ያስቀራል፡፡ በስደት የሚገኙ ኤርትራውያንም ወደ አገራቸው እንዲመለሱ መልካም አጋጣሚ ይፈጥራል፡፡

መልካም ግንኙነት መፍጠር ለሁለቱም አገራት ትልቅ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ አለው። ከአንድ መቶ ሚሊዮን ሕዝብ በላይ ያላት ኢትዮጵያ ለኤርትራ ሰፊ የገበያ መዳረሻ ትሆናለች፡፡ በዚህም ኤርትራ ከኢትዮጵያ የተለያዩ ምግብና ምግብ ነክ ያልሆኑ ሸቀጦችን በመግዛት ለዜጎቿ በቀላሉ ማቅረብ ትችላለች፡፡ መሠረተ ልማቶችን በማስፋፋት የንግድ ልውውጣቸውን ያጠናክራሉ፡፡ ኢትዮጵያ የኤርትራ ወደቦችን የምትጠቀምበትን ሠፊ ዕድል ያመቻቻል፡፡

አገራቱ በጠላትነት ከመፈራረጅ አልፈው በቀጣናው ሠላምና ፀጥታን ለማስከበር በጋራ የሚንቀሳቀሱበትን መልካም ሁኔታ ይፈጥራል፡፡ በምሥራቅ አፍሪካ በተለይም በሶማሊያ የነገሰውን የአሸባሪዎች ዕኩይ ድርጊት ለመግታትና የጥፋት እንቅስቃሴውን ለመመከት ትልቅ አቅም ይሆናል፡፡ ከኢትዮጵያና ከኤርትራ አልፎ ሰፊ ማህበራዊና ባህላዊ እሴት የሚጋሩት እንደ ጅቡቲና ሶማሊያ ያሉ አገራትን ጨምሮ ጠንካራ አካባቢያዊ ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት ለመዘርጋት ያስችላል፡፡

ከምንም በላይ ግን የሁለቱን አገራት በደም የተሳሰረ ግንኙነት ለማጠናከር ፋይዳው እጅጉን የጎላ ነው፡፡ አሁን በሁለቱ አገራት የተጀመረው ተግባራዊ እርምጃ በደንብ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት፡፡ የሠላም ሂደቱና ግንኙነቱ በሚፈለገው ደረጃ ለስኬት እንዲበቃ እንደ ጅማሮው ሁሉ አገራቱ በቀጣይ ሂደቱ ላይም በደንብ መሥራት አለባቸው፡፡ በሠላምና ልማት የታጀበ የጋራ ጉዞውን ዕውን ለማድረግ ሠላማዊ ትግሉ ተጠናክሮ ጥረቱ ለፍሬ እንዲበቃ መትጋት ተገቢ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት (ርዕሰ አንቀፅ )

No comments:

Post a Comment