Saturday, December 09, 2017

በግብጽ ያለው የውሃ ስጋት በእኛ ዘንድ ካለው ድህነት አይበልጥም!

(Dec 09, ( ርዕሰ አንቀፅ))--በ1970ዎቹ በኢትዮጵያ በተከሰተው ድርቅ ምክንያት አገሪቷ በታሪኳ ካጋጠሟት ሁሉ የከፋው ረሀብ ተከስቶ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ዜጎቿ በረሀብ አለንጋ ተቀጥተው ህይወታቸውን አጥተዋል። ዓለም ዛሬም ድረስ የማይረሳውና እስከ መዝገበ ቃላት ማጣቀሻ የደረሰ የረሀብ ታሪክ ጥሎብን ያለፈውም ይሄው የ1977ቱ ረሀብ ነው። ረሀቡ የተከሰተው በዝናብ ጥገኛ የሆነው ግብርና በዚያን ዘመን ላይ ባጋጠመው የዝናብ መስተጓጎልና በተፈጠረው ድርቅ ምክንያት ነበር።

በዚህ የድርቅ አደጋ ምክንያት የአባይ ወንዝም ከፍተኛ የሆነ የውሃ መቀነስ አጋጥሞት ስለነበር ግብጾች ስጋት ውስጥ ወድቀው ነበር። ድርቁ ወደ ረሀብ ተቀይሮና ኢትዮጵያውያን የሚበሉት አጥተው ለልመና ሲማጸኑና ሲረግፉ፤ ግብጾች የውሃ እጥረት ቢያጋጥማቸውም በአስዋን ግድብ ምክንያት ከከፋ አደጋው ተርፈዋል። በደህና ቀን የገነቡት ግድባቸው ከአስከፊ የረሀብ አደጋ ታድጓቸዋል። ከዚያ ዘመን በኋላም በኢትዮጵያ በተከሰቱ የድርቅ አደጋዎች ምክንያት ግብጽ የውሃ እጥረት ቢያጋጥማትም ስትራብ፣ ስትታረዝና እርዳታ ስትጠይቅ አልታየችም። ምክንያቱም ታላቁ የአስዋን ግድብ አላትና።

ኢትዮጵያውያን ግን ከ1977ቱም በተጨማሪ በየ10 ዓመቱ በተደጋጋሚ በድርቅ ተመትታለች፤ በረሀብ አለንጋ ተቀጥታለች፤ ለምናለች፤ ተመጽውታለች። ምክንያቱም ለግብጽ የድርቅ አደጋ መከታ የሆነውን የአባይ ወንዝ በጉያዋ ብትይዝም የራሷን አደጋ የምትመክትበት የአስዋን አይነት ግድብ የላትምና ነው።

ስለሆነም የበይ ተመልካች ሆና መኖር ግዴታዋ ነበር። ትናንት ዛሬ አይደለም፤ ነገም ዛሬ አይሆንምና ዛሬ ኢትዮጵያ በተሻለ የኢኮኖሚና ማህበረ ፖለቲካ ደረጃ ላይ ደርሳለች። በዚህም ምክንያት በእጇ ያለ ሀብትን ሁሉ አሟጥጣ ለመጠቀም ጉዞ ጀምራለች። ይህ ጉዞ የተጀመረው ከ26 ዓመታት በፊት ነው። በ26 ዓመታት ውስጥ መጓዝ የተቻለውን ያህል ተጉዘናል፤ የመጣነው ከምንሄደው አንጻር ብዙም አንገትን ቀና የሚያደርግ ባይሆንም እንዳለፉት ዘመናት ግን አንገት የሚያስደፋ ገበና የለብንም።

እንደ አገር ከላያችን ላይ አራግፈን ያልጨረስነው ድህነት ብዙ ጥረት፣ ብዙ ልማት፣ ብዙ ግድብ ይፈልጋል። ስለሆነም እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አይነቶች በብዛትም በጥራትም ያስፈልጉናል። ይሄንን ግድብ አትገንቡ ማለት በድህነት ውስጥ ቆዩ ማለት ስለሚሆንብን እንደ አገር ለዚህ አይነቱ ምክርም ይሁን ተግሳጽ ጆሮ የለንም። አይኖረንምም።

ግብጾች ዛሬም ድረስ ማመን ያቃታቸው የናይል ወንዝ የእነሱ ብቸኛ ሀብት አለመሆኑን ነው። ይህ ወንዝ የ10 የተፋሰሱ አገራት የጋራ ሃብት ነው። ስለሆነም ቢቻል በጋራ ካልተቻለ ደግሞ የወንዙ ባለቤቶች ሀብታቸውን በተናጠል የማልማትና የመጠቀም መብት እንዳላቸው መታወቅ አለበት። ይሄን እውነታ ግብጾች ያጡታል ማለት ራስን ማሞኘት ነው። ይልቁንም አውቆ የተኛን ሆኖባቸው እንጂ።

ግብጾች ለዘመናት በኖረው ፕሮፓጋንዳቸው «ግብጽ ያለ ናይል መኖር አትችልም» የሚለው ስብከታቸው አሁን ጊዜው አልፎበታል። በተቃራኒው የናይል ወንዝ አመንጪ አገራት ያለ ወንዙ መኖር አይችሉም የሚባልበት ደረጃ ላይ እንደደረስን ማወቅና መረዳት አለባቸው። የግብጽ ኢኮኖሚ እርሷ እንደምትለው በግብርና ላይ የተንጠለጠለ አይደለም።

ግብርና ያለው ድርሻ ከ13 በመቶ አይዘልም። እንደ ኢትዮጵያ ያሉ የተፋሰሱ አገራት ኢኮኖሚ ግን በግብርና ላይ ያለው ጥገኝነት እስከ 80 በመቶ የሚደርስ ነው። ስለሆነም የአባይ ወንዝ ከግብጽ ይልቅ ለኢትዮጵያ በጣም አስፈላጊ መሆኑን በዚህች ቁንጽል ማስረጃ ብቻ መመልከት ይቻላል።

መሬት ላይ ያለው እውነታ ይሄም ሆኖ ግን ኢትዮጵያ ወንዙን ብቻዬን ልጠቀምበት አላለችም። ቢቻል በጋራ አልምተን በጋራ እንጠቀምበት፤ ካልተቻ ግን የመጠቀም መብቴ ላይ ማንም ከፊቴ ሊቆም አይገባም ነው የምትለው። ግብጾች አብረው መዋኘት አይችሉም፤ መስመጥ እንጂ። ዘመኑ ደግሞ አብሮ መዋኘትና ሻምፒዮን የሚኮንበት ነው። ይህ ግን ለግብጽ አይሠራም።

ዛሬም ድረስ የቅኝ ግዛት ውልን ይዘው አደባባይ ይወጣሉ፤ ለድርድርም ይቀርባሉ። ይሄ ለግብጽ ህዝብ ውርደት ነው። የቅኝ ግዛት ውልን ይዞ መብቴ ይከበርልኝ ማለት አገሪቷን ከቅኝ ግዛት ነጻ ለማውጣት በአንድም በሌላም ዋጋ የከፈሉ የአገሪቷን ባለውለታዎች ሁሉ መክዳትና ውለታቸውን አፈር ላይ መጣልም ነው። ስለሆነም ግብጽና ግብጻዊያን ቅኝ ግዛት ትክክል ነው ከሚለው አቋማቸው ሊወጡ ይገባል።

በግብጽ ያለው የውሃ እጥረት ይከሰትብኛል ስጋት በኢትዮጵያ ካለው ድህነት አይበልጥም። የእነሱ ስጋት ገና ወደፊት ውሃ እጥረት ሊያጋጥመን ይችላል የሚል ነው። ይሄ እንደማይሆን ደግሞ በግልጽ ይታወቃል። የእኛ ድህነት ግን ወደፊት የሚከሰት ሳይሆን አብሮ ያለ ነው። ይሄን ድህነት ማሸነፍ ካለብን ግድቡ አንዱ መሳሪያችን ስለሆነ ያለማንም እገዛ 63 በመቶ እንዳደረስነው ሁሉ ያለማንም እገዛና ይሁንታ ከዳር እናደርሰዋልን።

ምክንያቱም የአንድ ግብጻዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ ሶስት ሺህ 514 ዶላር፤ ሆኖ የአንድ ኢትዮጵያዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ ገና 800 ዶላር እንኳን ያልደረሰው አንድም የተፈጥሮ ሀብትን በአግባቡ ከመጠቀም እና ካለመጠቀም ጋር የሚያያዝ ስለሆነ፤ ይሄ ልዩነት መስተካከል ካለበት ግድባችን መገንባቱ ልክም መብትም ነው!
ኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

No comments:

Post a Comment