Saturday, October 22, 2016

የቤተክርስቲያኗ አመራሮች ምዕመኑን በማስተማር ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ አሳሰቡ

(ጥቅምት 12፣ 2009))--በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች ከመንፈሳዊ ተግባራት ጐን ለጐን ስለ ሰላም፣ ፍቅርና የሀገር ዕድገት ምዕመኑን በማስተማር ረገድ የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ ፓትሪያሪክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ አሳሰቡ፡፡

የቤተክርስቲያኗ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እየተካሄደ ነው፡፡
በዚህ ወቅት የቤተ-ክርስቲያኒቱ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት  የኃይማኖት አባቶች የሕዝብን አንድነት የሚያስጠብቁ፣ እርስ በእርስ የሚያስማሙና የሚያግባቡ ትምህርቶችን እንዲያስፋፉ መክረዋል።

"የኃይማኖት አባቶች ለምእመኑ ማስተማር ያለባቸው ሰላምን የሚሰብከውን ምንም ያልተቀላቀለበትን የፈጣሪ ቃል ሊሆን ይገባል'' ብለዋል፡፡ 'የፈጣሪ ቃል ሁሉንም ያስማማል፣ ሁሉንም ያግባባል በመስማማት ላይ የተመሰረተ የአንድነትና የሰላም ፍሬን ለማፍራት ያስችላል'' ነው ያሉት፡፡

በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ የተከሰቱ ግጭቶችና ሁከቶች ተፈቃቅረውና ተዋደው ለዘመነት በአንድነት የኖሩትን ሕዝቦች እርስ በእርስ እንዲቃቃሩ ሲያደርግ እንደሚስተዋልም ጠቁመዋል፡፡ እንደ ፓትሪያርኩ ገለጻ "በተፈጠረው ግጭት የሰው ህይወት ጠፍቷል፣ ንብረት ወድሟል፣ በርካቶች ያለስራ ቀርተዋል፣ በሕዝቦች መካከልም የሕሊና ስብራት ተፈጥሯል"።

በዚህም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያን በተፈጠረው አሳዛኝ ክስተት ጥልቅ ሀዘን ተሰምቷታል ብለዋል።
ሰላሙ አስተማማኝ እስኪሆን አባቶች ሰፊ ስራ እንደሚጠበቅባቸው ያመለከቱት አቡነ ማትያስ ጉባኤው በሰላም፣ በልማት ሥራ መስፋፋትና በስብከተ ወንጌል መጠናከር ላይ ተወያይቶ ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ጠቁመዋል፡፡ 
ምንጭ ኢቢሲና ኢዜአ

No comments:

Post a Comment