Friday, March 13, 2015

ኢትዮጵያ የመካከለኛ ምሥራቅ አገራትን የግብርና ምርቶቿ የገበያ መዳረሻ ለማድረግ እየሰራች ነው

(መጋቢት 2/2007, (አዲስ አበባ))--ኢትዮጵያ የመካከለኛ ምሥራቅ አገራትን የቁም እንሰሳትና የግብርና ምርቶቿ የገበያ መዳረሻ ለማድረግ ዓልማ እየሰራች ነው። የንግድ ሚኒስቴር ለኢዜአ እንደገለጸው ሳውዲ ዓረቢያና የተባበሩት ዓረብ ኢሜሬቶች ለእነዚህ ምርቶች ተመራጭ የንግድ መዳረሻ አገራት ሆነዋል።

የሚኒስቴሩ የሁለትዮሽና አካባቢያዊ የንግድ ግንኙነትና ድርድር ዳይሬክተር አቶ ይሳቅ ተካልኝ እንደገለጹት ሳውዲ ዓረቢያ 35 በመቶ እንዲሁም የተባበሩት ዓረብ ኢሜሬትስ 17 በመቶ የመስኩን የኢትዮጵያ ምርት በማስገባት ግዙፍ የመዳረሻ አገራት ናቸው። ኢትዮጵያ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አገራት በዋናነት የቁም እንስሳት፣ ቡና እና ሰሊጥ የምትልክ ሲሆን ባለፉት አራት ዓመታት 11 ነጥብ 45 ቢልዮን የአሜሪካ ዶላር የሚያወጡ የግብርና ምርቶችን ልካለች።

አብዛኛው የአካባቢው አገራት በውኃ እጥረትና የባህር ውኃ የጨው መጠኑን ለመቀነስ የሚጠይቀው ወጪ ከፍተኛ መሆኑን ተከትሎ ለምግብነት የሚጠቀሙት የግብርና ምርቶች ከውጭ አገራት ለማስገባት ይገደዳሉ። ሳዑዲ ዓረቢያን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2014  3 ሚሊዮን ቶን ምግብ ከውጭ ያስገባች ሲሆን አገሪቷ በዚሁ ዓመት ስንዴን በማስገባት ከዓለም ስድስተኛዋ ከፍተኛ አገር ሆናለች።

ይህም ለአፍሪካ በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ በተለይ ባላቸው እምቅ አቅምና መልከዓ ምድራዊ ቅርበት ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው። በአካባቢው አገራት የምግብ ሸቀጦች ተፈላጊነት ከፍተኛ መሆኑን መንግሥት ተገንዝቦ ወደዚህ ክፍለ አሕጉር የሚላከውን ምርት በዓይነትና በመጠን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ ለቀጣናው አገራት ካላት ቅርበት ባሻገር ለም መሬትና ሰፊ የውኃ ኃብት ባለቤት መሆኗ ለመካከለኛው ምሥራቅ አገራት የምግብ ሸቀጦችም አቅራቢና ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ አገር ያደርጋታል።

አቶ ይሳቅ እንደገለጹት ኢትዮጵያ ባለፉት አምስት ዓመታት ወደ መካለለኛው ምሥራቅ አገራት በምትልካቸው የግብርና ምርቶች በመጠንና በዓይነት እድገት መጥቷል። ባለፉት አራት ዓመታት ኢትዮጵያ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አገራት ከላከችው የግብርና ምርት 2 ነጥብ 191 ቢልዮን የአሜሪካ ዶላር አጠቃላይ ገቢ አግኝታለች።

ኢትዮጵያ ወደ ውጭ ከላከችው ምርት አንፃር ሲታይ እስያ አገራት የአንበሳውን ድርሻ ሲይዙ ከዚህ ውስጥ የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ላቅ ያለ ድርሻ ይይዛሉ። አቶ ይሳቅ እንደገለጹት መንግሥት ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ከሚልከው ምርት የሚያገኘው ገቢ ለማሳደግና ከቀጣናው ጋር ያለውን የሁለትዮሽ የንግድ ግንኙነት ለማሳደግ እየሰራ ነው።

በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ዘመኑ ወደ መካከለኛው ምስራቅ ከተላኩ  የግብርና ምርቶች ቡና 9 በመቶ፣ ስጋና ሰሊጥ 5 ነጥብ 19 በመቶ ድርሻ ይዘዋል። የሞሀመድ ሁሴን ዓሊ አል ሙዲ ንብረት የሆነው ሳውዲ ስታር የግብርና ልማት ማህበርን ጨምሮ በርካታ የመካከለኛው ምሥራቅ ኩባንያዎች  በኢትዮጵያ ባለው ሰፊ የግብርና ኢንቨስትመንት ተሰማርተዋል።

ባለፉት አምስት ዓመታት በሳውዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኦሚሬትስና ኩዌት ኩባንያዎች ባለቤትነት አምስት ፕሮጀክቶች ፍቃድ አግኝተዋል።
ምንጭ:  ኢዜአ

No comments:

Post a Comment