Monday, February 16, 2015

«ምዕመናን ዐብይ ጾምን ማሳለፍ ያለባቸው የተቸገሩትን በመርዳትና መልካም ተግባራትን በማከናወን ሊሆን ይገባል» -የሃይማኖት አባቶች

(የካቲት 09/2007 , (አዲስ አበባ))--ምዕመናን ዐብይ ጾምን ማሳለፍ ያለባቸው የተቸገሩትን በመርዳትና መልካም ተግባራትን በማከናወን ሊሆን እንደሚገባ የሃይማኖት አባቶች አሳሰቡ። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንና የኢትዮጵያ የካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የሃይማኖት አባቶች የዐብይ ጾምን ምክንያት በማድረግ መግለጫ ሰጥተዋል።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትሪያሪክ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የእምነቱ ተከታዮች ከዛሬ ጀምሮ ለቀጣዮቹ 55 ቀናት የሚቆየውን የዐብይ ጾም ሲጾሙ የተቸገሩትን በመርዳትና መልካም ተግባራትን በማከናወን መሆን ይገባዋል።

''አንደበታቸውም ሃይማኖትን፣ ሰላምን፣ ፍቅርን፣ አንድነትንና ወንድማማችነትን የሚሰብክ መሆን ይገባዋል፤ በአገሪቱ ያለውን የሃይማኖት መቻቻል ቀጣይነት እንዲኖረው የሃይማኖቱ ተከታዮች የበኩላቸውን መወጣት አለባቸው" ብለዋል።

የጾም ወራት ከየትኛውም ጊዜ በበለጠ የሥራ ጊዜ መሆኑን የጠቆሙት ብጹዕ አቡነ ማትያስ፤ ከመንፈሳዊ ክንዋኔዎች ባሻገር አማኞች በልማታዊ ሥራዎች ላይ በስፋት የሚሳተፉበት ሊሆን ይገባል። በተለይ የአረንጓዴ ልማቱ፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራው በጾሙ ወራትም ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በማድረግ አገሪቱ የተፈጥሮ ጸጋዋ የተጠበቀ፣ ጽዱና ለኑሮ ምቹ ማድረግ እንደሚገባም ነው ያሳሰቡት።

የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን የባህርዳር ደሴት ሀገረ ስብከት ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ልሳነ ክርስቶስ ማቲዎስ በበኩላቸው፤ "የጾሙ አስተምህሮ የሚያመለክተው ፍቅርንና መተሳሰብን እንደመሆኑ መጠን ምዕመናን የተገለሉትን፣ የተናቁትን በድህነት ውስጥ ያሉትን ማሰብ ይኖርባቸዋል" ብለዋል።

ጾሙ ከምግብ የመከልከል ጾም ብቻ መሆን አይኖርበትም ያሉት ብጹዕ አቡነ ልሳነ፤ "የእምነቱ ተከታዮች ወንድሞቻቸውንና እህቶቻቸውን በመደገፍና ያላቸውን በማካፈል ፍቅራቸውን በተግባር ማሳየት ይጠበቅባቸዋል" ብለዋል።

ምዕመናን የታሰሩትን፣ የታመሙትን፣ የተጣሉትን ከማሰብ ባሻገር በአገር ደህንነት ጥበቃ የተሰማሩትን፣ የአገር መሪዎችን፣ የሃይማኖትና የህዝብ አገልጋዮችን በጸሎታቸው ሊያስቡ እንደሚገባ ጥሪ አቅርበዋል።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ
 Home

No comments:

Post a Comment