Sunday, January 18, 2015

በኢቦላ ሳይሆን በጭንቅላት ወባ መሞቱ የተረጋገጠው ግለሰብ የቀብር ሥነሥርዓት ተፈጸመ

(ጥር 9/2007, (አዲስ አበባ))-- በኢቦላ ተጠርጥሮ ክትትል ሲደረግለት የቆየውና በጭንቅላት ወባ መሞቱ የተረጋገጠው ኢትዮጵያዊ የደም ናሙና ደቡብ አፍሪካ ተልኮ ውጤቱ በአገር ውስጥ ከተደረገው ምርመራ ጋር ተመሳሳይ ሆኖ በመገኘቱ አስከሬኑ ለቤተሰቦቹ ተሰጠ። በተመሳሳይም በአካባቢያቸው ተገልለው በጊዜያዊነት እንዲቆዩ የተደረጉት ሰዎችም ወደ ህብረተሰቡ እንዲቀላቀሉ መደረጉ ተገለጸ።

በዓለም አቀፍ የግብረ ሰናይ ድርጅት ተቀጥሮ ወደ ሴራሊዮን አቅንቶ የነበረውና ወደ ሀገሩ ከተመለሰ ወዲህ ትኩሳት ታይቶበት አቅሉን በመሳቱ(ኮማ ውስጥ በመግባቱ)ክትትል ሲደረግለት የቆየው ግለሰብ ሕይወቱ ያለፈው በኢቦላ ቫይረስ አለመሆኑ በአገር ውስጥ በተደረገ የደም ምረመራ ተረጋግጦ እንደነበር ይታወሳል። ይህም ሆኖ በውጤቱ ላይ ይበልጥ እርግጠኛ ለመሆን «የደም ናሙናው ወደ ደቡብ አፍሪካ ተልኮ ግለሰቡ በኢቦላ ቫይረስ አለመሞቱ ተረጋግጧል» ሲል የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ትናንት በድረ ገጹ ላይ ባወጣው መረጃ አስታውቋል። ይሄንን ውጤት ተከትሎም ለሟች ቤተሰቦች ሳይሰጥ የቆየው አስከሬን ትናንትናውኑ ተሰጥቶ የቀብር ሥነ ሥርዓቱ መፈጸሙን ድረ ገጹ አስታውቋል።

በሚኒስቴሩ የኢቦላ መከላከል ግብረ ኃይል አባላት የሆኑት በኢትዮጵያ የህብረተሰብ ጤና ኢኒስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ዳዲ ጂማ እና በፌዴራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሚኒስትሩ አማካሪ ዶ/ር መርዓዊ አራጋው የሰጡትን መግለጫ ጠቅሶ መረጃውን ያወጣው ድረ ገጹ እንደዘገበው፤ ኢትዮጵያ ኢቦላን ለመከላከል ዘርፈ ብዙ ተግባራት እያከናወነች ነው። በተለይ የቫይረሱን ምንነት ለማረጋገጥ ያቋቋመችው ላቦራቶሪ እና የባለሙያዎቹን ብቃት በግለሰቡ ላይ በተደረገው ምርመራ ማረጋገጥ መቻሉ እንደ ጠንካራ ጎን ይወሰዳል።

ቀደም ሲል በድጋሚ ለማረጋገጥ የግለሰቡ የደም ናሙና ወደ አሜሪካ እንደሚላክ የተገለጸ ቢሆንም አሜሪካ ለመድረስ የሚወስደውን ረጅም ጊዜ፣ የምርመራ ውጤቱ እስኪታወቅ ከግለሰቡ ጋር ግንኙነትና ንክኪ የነበራቸው ሰዎችን አ

ግልሎ ማቆየቱ ብዙ ጊዜ እንዳይፈጅ በማሰብ በአጭር ጊዜ ውጤቱ ሊገለጽ ወደተቻለበት ደቡብ አፍሪካ መላኩን ጠቁሞ፤ ውጤቱም በፍጥነት መታወቁን መግለጻቸውን የድረ ገጹ ዘገባ ያስረዳል።

ወደ ደቡብ አፍሪካ የተላከው የሟቹ የደም ናሙና ውጤት በአጭር ጊዜ በመታወቁም ከአካባቢያቸው እንዳይንቀሳቀሱ ተደርገው የነበሩት ሰዎች ወደ መደበኛ ተግባራቸው እንዲገቡ መደረጉ ታውቋል።

የአካባቢ ጤና ስፔሻሊስት (ባለሙያ) የነበረው ሟቹ ግለሰብ በራሱ የግል ጥረት በአንድ የውጭ ድርጅት ተቀጥሮ ወደ ሴራሊዮን ሊሠራ የሄደ እንደነበርና ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሰ በኋላም ከቦሌ አየር ማረፊያ ጀምሮ ጠንካራ ክትትል ሲደረግበት እንደቆየ ታውቋል።

የፌዴራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በግለሰቡ ሞት ምክንያት የተሰማውን ኀዘን ለቤተሰቦቹ የገለጸ ሲሆን፤ ሐሙስ ዕለትም የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ከፍተኛ ኃላፊዎችና ሌሎች ባለሙያዎች በአካባቢያቸው ተገልለው በጊዜያዊነት እንዲቆዩ የተደረጉትን ሰዎችን በአካል ተገኝተው ማፅናናታቸውንና ማረጋጋታቸውን የድረገጹ ዘገባ ያሳያል።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

Related topics:
በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የኢቦላ ምርመራ እየተካሄደ ነው
በኢቦላ ተጠርጥሮ ክትትል ሲደረግበት የቆየው ኢትዮጵያዊ ትናንት አረፈ
Ethiopia to deploy health professionals to Ebola-stricken ...
Ethiopian health workers arrive in Liberia to help fight Ebola
Ebola Scares Prevent Oklahoma Students ...
Kenya, Ethiopia boost anti-Ebola measures  

No comments:

Post a Comment