Monday, January 12, 2015

በአገራቸው ኢንቨስት ለሚያደርጉ ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል

(ጥር 3/2007, (አዲስ አበባ))--መንግሥት በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለሚያደርጉ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ገለጹ።

አቶ ሬድዋን በአገራቸው በኢንቨስትመንት መስክ መሰማራት የሚፈልጉ ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራ ወክሎ የከመጣው ቡድንና በአገር ውስጥ የሚኖሩ ተመላሽ ዳያስፖራዎችን ዛሬ ተቀብለው አነጋግረዋል።

በዚሁ ጊዜ ሚኒስትር ሬድዋን እንደገለጹት በውጭ አገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች የአገሪቱን ዕድገት ለማፋጠን እየተደረገ ባለው ሁሉን አቀፍ ጥረት የሚያጋጥሙትን ችግሮች በጋራ እየፈቱ ማስቀጠል ይጠበቅባቸዋል።

"መንግሥት ከዳያስፖራው ማኅበረሰብ ተቀራርቦ ለመስራት ዝግጁ ነው" ያሉት አቶ ሬድዋን "በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በአገራዊ ልማት ለሚኖራቸው ተሳትፎ መንግሥት ይደግፋል" ብለዋል። በአገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ የሚያጋጥሙ ችግሮችን ሁሉም ወገን እጅ ለእጅ ተያይዞ በመረባረብ ማስወገድና ልማቱን ማስቀጠል እንደሚገባ ነው ሚኒስትሩ የተናገሩት።  

በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዳያስፖራ ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ፈይሰል አልየ በበኩላቸው መንግሥት የዳያስፖራ ማኅበረሰብ የሚያደርገው የልማት ተሳትፎ ያለ አንዳች ችግር እንዲቀጥል በውስጥና በውጭ አገር የሚገኙ ሚስዮኖች እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።

በውጭ የሚገኙና በአገራቸው ኢንቨስት ለማድረግ የተዘጋጁ 300 ዳያስፖራዎችን በመወከል ንግግር ያደረጉት አቶ እስራኤል ገደቡ እንደገለጹት በማህበራዊ ሚዲያ ለ13 ዓመታት የአገራቸውን ገጽታ ለዓለም ሲያስተዋውቁ እንደነበር ጠቅሰዋል።

አሁን ደግሞ ኃብትና ዕውቀታቸውን በአገራቸው ለማፍሰስ ከመንግሥት ጋር እየተጋገሩ መሆናቸውን ነው የገለጹት። ተመላሽ ዳያስፖራና በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በምጣኔ ኃብት ረዳት ፕሮፌሰር ተሾመ አዱኛ በበኩላቸው ዳያስፖራው በውጭ ባካበተው ኃብትና ዕውቀት አገሩንና ወገኑን ለመርዳት ዝግጁ ነው ብለዋል።

አሁን በኢትዮጵያ የተረጋጋ ፖለቲካና ምቹ የኢንቨስትመንት ዕድል በመኖሩ በአገር ኢንቨስት በማድረግ የተጀመረውን ልማት በዘላቂነት ለማስቀጠል እንቅስቃሴ እያደረጉ መሆናቸውን ነው የተናገሩት።

ኢትዮጵያ ውስጥ በኢንቨስትመንት መስክ የተሰማሩ ወይዘሮ ወሰኔ ኃይሉ በአገር ውስጥ ለኢንቨስትመንት የተመቻቸ ሁኔታ በመኖሩ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልድ ኢትዮጵያውያን በአገራቸው ኢንቨስት በማድረግ አገራዊ እድገት እንዲያፋጥኑ ጠይቀዋል።

ከ40 ዓመታት በላይ በውጭ አገር የቆዩት ወይዘሮ ወሰኔ በአገራቸው ኢንቨስት በማድረግ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተረድተው የእሳቸውን አርአያ ሌሎች ዳያስፖራዎች እንዲከተሉ ጥሪ አቅርበዋል። በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵውያን ዳያስፖራዎችን በመወከል የመጣው ቡድን በኢትዮጵያ ቆይታው የተለያዩ ግዙፍ አገራዊ ፕሮጀክቶች ተዘዋውሮ እንደሚመለከት በዚሁ ጊዜ ተገልጿል።

እነዚህ በአገራቸው ኢንቨስት ለማድረግ የተሰባሰቡት 300 ዳያስፖራዎች ከ10 ዓመት በፊት ጀምሮ በማህበራዊ ሚዲያ በፓል ቶክ ስለ አገራቸው እየተወያዩና የአገራቸውን ገጽታ ለመገንባት በጋራ ሲሰሩ መቆየታቸውን ከመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት የተገኘ መረጃ ያመለክታል።
ምንጭ:  ኢዜአ 

No comments:

Post a Comment