Wednesday, November 05, 2014

የሻዕቢያ ድንበር ዘለል ደባዎች ዳግም ሲጋለጡ!

(Nov 05, 2014, (አዲስ አበባ))--የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት የሰየመው ኤርትራ ላይ የተጣለውን የጦር መሳሪያና የኢኮኖሚ ማዕቀብ የሚቆጣጠረው የሶማሊያና የኤርትራ ክትትል ቡድን ሰሞኑን ኤርትራን የሚመለከት ሪፖርት ይፋ አድርጓል። ሪፖርቱ የኤርትራ መንግሥት የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት የፈረጃቸውን ቡድኖች በገንዘብ፣ በጦር መሳሪያና በስልጠና እንደሚደግፍ አጋልጧል። በዚህ ፅሁፍ የዚህን ሪፖርት ይዘትና አንደምታውን በአጭሩ አቃኛለሁ። ከዚያ በፊት ግን ባለፉት አንድ ተኩል አስርት ዓመታት ያህል በኢትዮጵያና በኤርትራ መሃከል የነበረው ግንኙነት ምን እንደሚመስል ቢያንስ አሁን ለደረሱ ወጣቶች ለማስታወስ ያህል በመጠኑ ወደ ኋላ ተመልሼ መቃኘትን አስፈላጊ ሆኖ አግኝቼዋለሁ።

የኤርትራ መንግሥት ከአስራ ስድስት ዓመታት በፊት ኢትዮጵያ ላይ ግልፅ ወረራ ፈፅሞ ነበር። ወረራውን የፈፀመው ገና የነፃይቷ ኤርትራ ምሥረታ በወጉ ሳይፀና በእርጥቡ ሳለ ነበር። ተመስርቶ ግማሽ አስርት ዓመት እንኳን በወጉ ሳይሞላው ፤ በ1990 ዓ/ም በወርሃ ግንቦት ኢትዮጵያ ላይ ወረራ ፈፀመ። ይህ የኤርትራ መንግስት የፈፀመው ግልፅ  ወረራ ለኢትዮጵያ ያልተጠበቀና ድንገተኛ ነበር። ከረጅም ጊዜ ጦርነት ውስጥ ወጥታ ሊነገር በማይችል ደረጃ የተነኮታኮተውን ኢኮኖሚዋን እንዲያገግም በማድረግ ሕዝቧን በቀን ሦስቴ መመገብ መቻልን እንደ ራዕይ ይዛ አይኗን ገልፃ መንቀሳቀስ  እንደጀመረች የተፈፀመ ወረራ በመሆኑ አስደንጋጭም ነበር።

ወረራው እንደተፈፀመ የኢትዮጵያ መንግሥት ችግሩን በሰላማዊ መንገድ የመፍታት አማራጭን አስቀድሞ፣ በሰከነ አእምሮ ወረራውን ለመቀልበስ ይወስናል። የኤርትራ መንግስት በምክርም፣ በምልጃም . . . ሰላማዊ አማራጭን አሻፈረኝ በማለቱ ወረራውን በኃይል የመቀልበሱ አማራጭ ላይ ታላቅ ሀገራዊ መግባባት ተፈጠረ። የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ወረራውን ለመቀልበስ ከዳር እስከዳር በታላቅ ሀገራዊ መግባባት ተነቃነቁ።

የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች በዚህ ወረራውን ለመቀልበስ በወሰዱት እርምጃ በወረራ የያዘው ስፍራ ላይ እንደፋሮ መሬት ምሶ ማንም አይነካኝም በሚል እብሪት ሲታበይ የነበረው የኤርትራው ሻዕቢያ ሰራዊት እንደገለባ ተበተነ። በዚህ አኳኋን ኢትዮጵያ ወረራውን ቀልብሳ ሁኔታውን ቀድሞ ወደነበረበት መለሰች። ይህ የአዲሲቱ ኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች የሉዓላዊት ኢትዮጵያ ባለቤቶችና በእኩልነትና በመቻቻል ላይ የተመሰረተ ጥብቅ አንድነት ያላቸው መሆኑን ያረጋገጡበት የቅርብ ጊዜ ታሪካችን ነው።

ወረራው ከተቀለበሰ በኋላ የኤርትራ መንግስት ኢትዮጵያ ላይ ወረራ ለመፈፀም አነሳሳኝ የሚለው የድንበር ጉዳይ በዓለም አቀፍ ዳኝነት እልባት እንዲበጅለት ሁለቱ ሀገራት በአልጀርስ በተካሄደ ስምምነት ይዋዋላሉ። በዚህ መሰረት ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ውሳኔ ያሳልፋል። ኢትዮጵያ ውሳኔውን ሙሉ በሙሉ መቀበሏን አስታውቃ የድንበር ውሳኔው ሃሳባዊ በመሆኑ  መሬት ላይ ሲካለል አንድ አባወራን ሁለት ቦታ ሰንጥቆ እስከማቋረጥ የደረሰ አስቸጋሪ ሁኔታ ስላለው በውይይትና በምክክር እንዲከናወን ትጠይቃለች፤ ልብ በሉ ውሳኔውን አልቀበልም አላለችም።

በሌላ በኩል የኤርትራ መንግሥት ይህን ለችግሩ የመጨረሻ እልባት የሚያስገኝ አካሄድ አልቀበልም አለ። ይህ አልበቃ ብሎት በሁለቱ ሀገራት መሃከል ግጭት እንዳያገረሽ ወረራውን በቀሰቀሰው የኤርትራ ድንበር ሃያ አምስት ኪሎ ሜትር ርቀት ውስጥ ሰፍሮ የነበረውን የተባበሩት መንግስታት ሰላም አስከባሪ ኃይል አስወጣ። እነዚህ እውነታዎች የኤርትራ መንግስት በሁለቱ ሀገራት መሃከል የተፈጠረው አለመግባባት ፍፁም የሆነ ሰላማዊ መፍትሄ እንዲበጅለት ፍላጎት የሌለው መሆኑን በግልፅ ያሳያሉ።

እንግዲህ የኤርትራ መንግሥት የፈፀመው ወረራ ሙሉ በሙሉ ከተቀለበሰ አስራ አምስት ዓመታት ገደማ አስቆጥሯል። በእነዚህ አመታት ውስጥ የኤርትራ መንግሥት ኢትዮጵያ ላይ ዳግም ወረራ መፈፀም አልቻለም። ወረራ ከመፈፀም የተቆጠበው ወረራ መፈፀም ስለማይፈልግ ወይም ለዓለም አቀፍ ሕጎች ተገዢ ስለሆነ ሳይሆን  ኢትዮጵያ ላይ ወረራ መፈፀም የሚያስችል አቅም ስለሌለው ነው። ይሁን እንጂ በሰርጎ ገቦች አማካኝነት ጥቃት ለመፈፀም ተደጋጋሚ ሙከራ አድርጓል። በሁለቱ አገራት ድንበር አቅራቢያ በጉብኝት ላይ የነበሩ የውጭ ሀገራት ቱሪስቶች ላይ ተፈፅሞ የነበረውን ጠለፋ ለዚህ አስረጂነት መጥቀስ ይቻላል። ይህንንም የጥቃት ስልት የሚያዛልቅ ሆኖ አላገኘውም።

የኤርትራ መንግሥት ኢትዮጵያን ለማጥቃት ከተጠቀመበት የእጅ አዙር መንገድ ቀዳሚውና እስከ አሁንም የሚከተለው፣ አልሸባብ የተባለውን በሶማሊያ ውስጥ የሚንቀሳቀሰውን ዓለም አቀፍ አሸባሪ ቡድንና በተለያየ ምክንያት ሕገመንግሥታዊው ሥርዓቱ ያልተመቻቸውን ኢትዮጵያውያን ቡድኖች አደራጅቶ፣ አሰልጥኖና አስታጥቆ ለሽብር ጥቃት ወደኢትዮጵያ ማሰማራት ነው።

የኤርትራ መንግሥት አልሸባብ የተሰኘውን ዓለም አቀፍ አሸባሪ ቡድን በጦር መሳሪያ እንደሚረዳ በማስረጃ በመረጋገጡ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት የጦር መሳሪያና የኢኮኖሚ ማዕቀበ የተጣለበት መሆኑ ይታወሳል። የአልሸባብን በዚሁ ልተወውና በኤርትራ መንግሥት የሚደገፉ መነሻቸው ኢትዮጵያ የሆኑ ሕገመንግሥ ታዊው ሥርዓት ያልተመቻቸው ቡደኖች ላይ ላተኩር።

ከእነዚህ መነሻቸውን ኢትዮጵያ ካደረጉ ቡደኖች መሃከል በኤርትራ መንግስት የገንዘብ፣ የመሳሪያና የስልጠና ድጋፍ እየተደረገላቸው ኢትዮጵያ ውስጥ የሽብር ጥቃት የመፈፀም ተልዕኮ ተቀብለው ከሚሰማሩት መሃከል የኦጋዴን ብሄራዊ ነፃነት ግንባር (ኦብነግ)፣ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)፣ ተጠቃሾቹ ናቸው። በአሜሪካ እንደሰብአዊ ድርጅት የተቋቋመው ግንቦት 7 የተባለው ቡድንም ኢትዮጵያ ላይ የሽብር ጥቃት ለመፈፀም ከኤርትራ ተልዕኮ ከሚቀበሉት ውስጥ ይገኝበታል። እዛው ኤርትራ የተደራጁ የትግራይ ብሄራዊ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄን የመሳሰሉ ቡድኖችም በኤርትራ ተልዕኮ አስፈፃሚነት ተሰልፈዋል።

ኦነግና ኦብነግ በኢፌዴሪ ሕገመንግሥት ላይ የራስን እድል በራስ የመወሰንን መብት በተመለከተ ከተደነገገው ውጭ የኢትዮጵያ ሶማሌንና የኦሮሚያ ክልሎችን በኃይል ገንጥለው ነፃ መንግሥት የመመስረት ዓላማ ይዘው የሚንቀሳቀሱ ቡደኖች ናቸው። እነዚህ ሁለት ቡድኖች ይህን ዓላማ ለመያዝ የሚያበቃ አንዳችም ምክንያት እንደሌላቸው ለመረዳት የኢፌዴሪ ሕገመንግሥት የብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች መብትን በተመለከተ የያዘውን ድንጋጌ መመልከት አስፈላጊ ነው።

የኢፌዴሪ ሕገመንግስት የብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች መብቶችን አስመልክቶ በአንቀፅ 39 ላይ ድንጋጌ አስፍሯል። በዚህ አንቀፅ “የብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች መብት” በሚል ርዕስ ሥር የሚከተለው ተደንግጓል፤

• ማንኛውም የኢትዮጵያ ብሄር፣ ብሄረሰብ፣ ሕዝብ የራሱን እድል በራሱ የመወሰን እስከመገንጠል ያለው መብቱ በማንኛውም መልኩ ያለገደብ የተጠበቀ ነው፤
• ማንኛውም የኢትዮጵያ ብሄር፣ ብሄረሰብ፣ ሕዝብ በቋንቋው የመናገር፣ የመፃፍ፣ ቋንቋውን የማሳደግ እና ባህሉን የመግለፅ፣ የማዳበርና የማስፋፋት እንዲሁም ታሪኩን የመንከባከብ መብት አለው፤
• ማንኛውም የኢትዮጵያ ብሄር፣ በሄረሰብ ሕዝብ ራሱን የማስተዳደር ሙሉ መብት አለው። ይህ መብት ብሄሩ፣ ብሄረሰቡ፣ ሕዝቡ በሰፈረበት መልክዓምድር ራሱን የሚያስተዳድርበት መንግሥታዊ ተቋማት የማቋቋም እንዲሁም በክልልና በፌዴራል አስተዳደሮች ውስጥ ሚዛናዊ ውክልና የማግኘት መብትን ያጠቃልላል።

ይሄው ሕገ-መንግሥት እስከመገንጠል የሚዘልቀው የራስን እድል በራስ የመወሰን መብት ተግባራዊ የሚሆንበት አግባብንም አስቀምጧል። ይህም በዚሁ በአንቀፅ 39 በንኡስ አንቀፅ 4 ላይ ከፊደል ተራ ሀ እስከ ሠ በሰፈሩት ድንጋጌዎች የተገለፀው ነው። እነዚህም፤

• የመገንጠል ጥያቄ በብሄር፣ ብሄረሰቡ ወይም በሕዝቡ የሕግ አውጭ ምክር ቤት በሁለት ሦስተኛ ድምፅ ድጋፍ ተቀባይነት ማግኘቱ ሲረጋገጥ፤
• የፌዴራል መንግሥት የብሄር፣ ብሄረሰቡ ወይም የሕዝቡ ምክር ቤት ውሳኔ በደረሰው በሦስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ለጠያቂው ብሄር፣ ብሄረሰብ፣ ሕዝብ ሕዝበ ውሳኔ ሲያደራጅ፤
• የመገንጠሉ ጥያቄ በሕዝበ ውሳኔው በአብላጫ ድምፅ ሲደገፍ፤
• የፌዴራል መንግሥት መገንጠሉን ለመረጠው ብሄር፣ በሄረሰብ ወይም ሕዝብ ምክር ቤት ሥልጣኑን ሲያስረክብ፤
• በሕግ በሚወሰነው መሰረት የንብረት ክፍፍል ሲደረግ የሚሉት ናቸው።

እንግዲህ ኦብነግና ኦነግ የኢትዮጵያ ሶማሌና የኦሮሚያ ብሄሮች ሕዝቦች የሚኖሩባቸውን ክልሎች መገንጠል የሚፈልጉት ከላይ የተገለፀውን ሕገመንግሥታዊ የራስን እድል በራስ የመወሰን እስከመገነጠል የዘለቀ መብትና መብቱ ተግባራዊ የሚሆንበትን ሥርዓት ባላገናዘበ ሁኔታ ነው።

የአንድ ብሄር ወይም ብሄረሰብ የመገንጠል ጥያቄ መነሻ ብሄራዊ ጭቆና ነው። የአንድ ብሄር ወይም ብሄረሰብ መገንጠል በራሱ መድረሻ ሳይሆን፣ ብሄራዊ መብትና ነፃነት ወደተረጋገጠበት ሥርዓት የሚወስድ የመጨረሻ አማራጭ ነው። ብሄራዊ ጭቆና በሌለበትና እንደማይኖር በህገመንግሥት በተረጋገጠበት ሁኔታ እስከመገነጠል በዘለቀ መብት ዋስትና በተሰጠውና ይህ የሚሆንበት ሥርዓት በግልፅ በተቀመጠበት ሁኔታ አንድ ቡድን የመገንጠል ጥያቄ ሊያነሳ የሚችልበትና ይህን ለማስፈፀም ብረት አንስቶ የሚዋጋበት አንዳችም ምድራዊ ምክንያት የለም።

አሁን የኢትዮጵያ ሶማሌና የኦሮሞ ብሄሮች ሕዝቦች ከብሄራዊ ጭቆና ነፃ ሆነው ራሳቸውን በራሳቸው እያስተዳደሩ፣ በመረጧቸው ሰዎች እየተዳደሩ፣ ልጆቻቸውን በቋንቋቸው እያስተማሩ፣ ቋንቋቸውን   እስከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ድረስ እንዲሰጥና እንዲጠና በማድረግ እያዳበሩ፣ ባህላቸውን እያጎለበቱ ታሪካቸውን እየተንከባከቡ . . . ከሌሎች የሀገሪቱ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ጋር በመከባበርና በእኩልነት እየኖሩ ይገኛሉ። ይህ በሕገመንግስት ተረጋግጧል፤ ዋስትናም ተሰጥቶታል።

ይህ ከላይ የተገለፀ እውነታ ኦብነግና ኦነግ በሃይል የመገንጠል ጥያቄ እንዲያነሱ የሚያደርጋቸው አንዳችም ምድራዊ ምክንያት እንደሌለ በግልፅ ያሳያል። የኢትዮጵያ ሶማሌና የኦሮሞ ብሄር ሕዝቦች የመገንጠል ጥያቄውን ሊያነሱ የሚችሉበት ሁኔታ አለ ቢባል እንኳን፣ ጥያቄው የሕዝብ ጥያቄ መሆኑን በሚያረጋግጥ ሁኔታ የሚከናወንበት ሥርዓት በሕገመንግሥቱ ተደንግጓል።

ኦብነግና ኦነግ ከዚህ የመገንጠል ጥያቄው የህዝብ መሆኑን ከሚያረጋግጥ ሕገመንግሥታዊ ሥርዓት ውጭ በሃይል ለመገንጠል ነው የሚንቀሳቀሱት። ልብ በሉ ሕገመንግሥቱ የብሄሮችንና ብሄረሰቦችን የመገንጠል መብትና ነፃነት አረጋግጧል። ሕገመንግስቱን እስከተቀበሉና እስካከበሩ ድረስ ቡድኖቹ አሁንም በሰላማዊ መንገድ የመንቀሳቀስ እድላቸው ክፍት ነው።

ሁለቱ ቡድኖች ይህን መብት ከመጠቀም ይልቅ በሃይል፣ በተለይ በአሸባሪነት ጥቃት መንግሥትና ሕዝብን በማንበርከክ የመገንጠል ጥያቄያቸውን ለማሳካት በመሞከር አካሄዳቸው ፀንተዋል። በመሆኑም የኢፌዴሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቡደኖቹን በአሸባሪነት ፈርጇቸዋል።

በዚህ ፅሁፍ መግቢያ ላይ እንደጠቀስኩት የኤርትራ መንግሥት ኢትዮጵያ ላይ ፈፅሞት የነበረው ግልፅ ወረራ ዳግም ወረራ መፈፀም እንደማይችል በሚያስተምር አኳኋን ከተቀለበሰ በኋላ ኢትዮጵያ ላይ ጥቃት ለመፈፀም በኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት የተፈረጁትን ኦብነግና ኦብነግን ይጠቀማል።

ይህ ቡድኖቹ የኤርትራ መንግስትን ኢትዮጵያን የማጥቃት ተልዕኮ ተቀብለው በተደጋጋሚ በፈፀሙትና በሞከሩት የሽብር ጥቃቶች ተረጋግጧል። የኢትዮጵያ ህዝብ ኦብነግና ኦነግ የኤርትራ መንግሥት ኢትዮጵያን ለማተራመስና ለማዳከም የሚጋልባቸው ፈረሶች መሆናቸውን ያለአንዳች ጥርጣሬ ያውቃል፤ የቡደኖቹ ደጋፊዎች የሆኑትም ቢሆኑ ይህን አይክዱም።

የኤርትራ መንግሥት ኢትዮጵያን ለማተራመስና ለማዳከም የሚጋልባቸው ኦብነግንና ኦነግን ብቻ አይደለም። ግንቦት ሰባት የተባለው ቡድንም የኤርትራ መንግሥት ይጋልበው ዘንድ ጀርባውን አደላድሎ አመራሮቹን ወደአሥመራ ቤተ መንግስት የላከው በተመሰረተ ማግስት ነበር።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment