Thursday, October 23, 2014

የማህፀን በር ካንሰር ያልተነገረለት ገዳይ በሽታ

(Oct 23, 2014, (አዲስ አበባ))--የካንሰር ዓይነቱ ብዙ ነው። የማህፀን በር ካንሰር ( Cervical cancer ) የሚባለው አንዱ ሲሆን ገዳይነቱ ከጡት ካንሰርም በላይ እንደሆነ ይነገርለታል።

የማህፀን በር ካንሰር ዕድሜያቸው 30 በደረሱና የግብረ ስጋ ግንኙነት በጀመሩ ማናቸውም ሴቶች ላይ ሊከሰት የሚችል፣ ነገር ግን በቀላሉ በቅድመ ካንሰር ምርመራ ሊታወቅና ህክምናም በአጭር ጊዜ

(Single Visit approch ) ውስጥ ሊደረግለት የሚችል በሽታ ነው። ሆኖም ብዙዎቹ የሀገራችን ሴቶች በማህፀን ካንሰር ጉዳይ ላይ ግንዛቤ ይዘው ወደ ህክምና ተቋማት እንደማይመጡ ነው የሚነገረው። እርግጥ ቀደም ባሉት ዓመታት የህክምና አገልግሎቱም የተስፋፋ ባለመሆኑ ጭምር የማህፀን በር ካንሰር ጥቃትን ለመከላከል ትኩረት ተደርጎ የተሰራው የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር «ፓስ ፋይንደር» ከተሰኘ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ጋር በጀመሩት ስራ ነው። የሲዲሲ(CDC) ወይም የአሜሪካ እርዳታ ድርጅት ድጋፍም ታክሎበት በሀገሪቱ በሚገኙ የተለያዩ ክልሎች ከ21 እስከ 23 በሚደርሱ ሆስፒታሎች አገልግሎቱ እየተሰጠ ነው።

የደቡብ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ደግሞ ተጨማሪ ትኩረት በመስጠት በራሱ አቅም በ9 ሆስፒታሎች አገልግሎቱን ለማዳረስ ጥረት እያደረገ መሆኑን ነው መረጃዎች የሚያሳዩት። «ባለፉት ሦስት ዓመታትም በናሙና ተቋማቱ 17 ሺ ሴቶች የማህፀን በር ካንሰር የጤና ምርመራ አድርገው 1500 የሚሆኑት ችግሩ የተገኘባቸው ሲሆን ከዚህ ውስጥ 90 በመቶው የሚሆኑት ዕርዳታ ተደርጎላቸዋል» የሚለው የጤና ጥበቃ ሚኒስትር የቅርብ ጊዜ መረጃ፤ ለመመርመር ከቻሉት ውስጥ ከ88 በመቶ የማያንሱት ሴቶች በሽታው ያልተገኘባቸው ዋነኛ ምክንያትም የተሰጣቸውን ግንዛቤ ጨብጠው ጤናቸውን ለመጠበቅ በወሰዱት እርምጃ እንደሆነ ጠቁሟል። በቀጣይም የፓስፋይንደርና ሌሎች አጋዥ አካላትን ጥረት በመንግስት አቅም ለማስፋት በመላው ሀገሪቱ 182 በሚደርሱ ሆስፒታሎች የምርመራና ህክምና አገልግሎቱን ለመስጠት ጥረት እንደሚደረግም ይጠቅሳል።

በቅርቡ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ሙያተኞች «የካንሰር ሚዲያ ፎረም»ን በመመ ስረት በሂደት ደግሞ ሁሉንም የመንግስትና የግል መገናኛ ብዙሃን ባካተተ አኳኋን ለመንቀሳቀስ ጥረት ጀምረዋል። እስከአሁን ከትግራይ፣ ከኦሮሚያና አማራ ክልል መገናኛ ብዙሃን፣ ከኢትዮጵያ ኘሬስ ድርጅት ፣ ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን፣ ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ፣ ከጤና ጋዜጠኞች ማህበር ወዘተ የተወከሉ አባላት ፎረሙን የመሰረቱ ሲሆን ብዙ ሳይነገርለት ሴቶችን ክፉኛ እያጠቃ ባለው የማህፀን በር ካንሰር ላይ ጠንካራ ዘመቻ ለማድረግ ነው እንቅስቃሴ የጀመሩት።

በሚዲያ ፎረሙ ምስረታ ላይ ሠሞኑን የተገኙት የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ አህመድ አሚኖ አሁንም በሀገራችን 51 በመቶ እናቶች ብቻ ወደ ሆስፒታል ሂደው ለመውለድ የሚጥሩ ሲሆን፤ ቀሪዎቹ 49 በመቶ የሚሆኑት ለህክምና ወደ ሆስፒታል እንደማ ይሄዱ ይገልጻሉ ። ይህ ሁኔታም የጤና መሠረተ ልማቱን ከማስፋት ባሻገር የእናቶችና ህፃናትን ጤና ለመታደግ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራ መሰራት እንዳለበት አመላካች ነው። የማህፀን በር ካንሰር ህክምናን በተመለከተም የመገናኛ ብዙሃን ሙያተኞች፣

የጤና ባለሙያዎችና ሁሉም ባለድርሻ አካላት ትኩረት ሰጥተው መስራታቸው ተገቢ መሆኑን አስምረውበታል። መንግስት በብሄራዊ ደረጃ በቀዳማዊ እመቤት ሮማን ተስፋዬ የሚመራ « ብሄራዊ የካንሰር ምክር ቤት» እንዲቋቋም አድርጎ ባለድርሻ አካላት በንቃት እንዲሳተፉ ማስቻሉም በበጎ የሚነሳ እንደሆነ አውስተዋል።

የካንሰር ህመም ተላላፊ ካልሆኑ ገዳይ በሽታዎች ተርታ የሚመደብ ሲሆን በሽታው ከሰው ልጅ አኗኗር ጋርም ይያያዛል። በተለይ አካላዊ እንቅስቃሴ አለማድረግ፣ የክብደት መጨመረና የደም ዝውውር አመቺነት መታጣት ፣ የአየር አጠቃቀምና አመጋገብ ሚና አላቸው ነው የሚሉት ሙያተኞች ። የማህፀን በር ካንሰርም በረጅም ጊዜ ጉዳት ሴቶች ለመውለድ እንዲቸገሩ ፣ ብሎም ለህልፈተ ህይወት እንዲዳረጉ የሚያደርግ በሽታ ነው።

በሽታው በማህፀን በር ላይ በሚያቆ ጠቁጥ ቫይረስ አማካኝነት ነው ሊነሳ የሚችለው። የማህፀን በር ቫይረስ በግብረ ስጋ ግንኙነትና በብልት አካባቢ ንክኪ በሚመጣ ጉዳት የሚባባስ ሲሆን ካለማድረግ ቢሻልም ኮንደም መጠቀምም ቢሆን ቫይረሱን እንደማ ያድነው ይነገራል። ስለሆነም ማንኛዋም ዕድሜዋ 30 የደረሰና ግብረስጋ ግንኙነት የጀመረች ሴት በቀላሉ ወደህክምና ተቋማት መሄድና መመርመር አለባት። ለምሣሌ እንደ ቤተሰብ መምሪያ ባሉ ተቋማት እስከ 50 ብር ብቻ በመክፈል ምርመራ ማድረግ እንደሚቻል ነው በወቅቱ የተገለጸው።

በፓስ ፋይንደርና በጤና ጥበቃ ትብብር በተጀመሩ የህክምና ተቋማትም በትግራይ፤ መቀሌ፣ አክሱምና ማይጨው ሆስፒታሎች ፣ በአማራ፤ ባህር ዳር፣ ደሴና ደብረማርቆስ፣ በኦሮሚያ፤ አሰላ፣ ቢሾፍቱና ነቀምት ህክምና እየተሰጠ ይገኛል። በደቡብ ክልል ግን የክልሉ መንግስትም የተሻለ ጥረት በማድረጉ ይርጋለም፣ አዋሳ ፣ ሶዶ፣ ዲላ፣ ቡታጅራ ፣ ሆሳዕና፣ አርባምንጭ፣ ተርጫ፣ ሚዛን አማን፣ ጊዴሎና ጅንካ ሆስፒታሎች አገልግሎቱ ተዘርግቷል።

እስከአሁን በዓለም ላይ በበሽታው እየሞቱ ካሉት ሴቶች ውስጥ 88 በመቶ የሚደርሱት በድሃ ሀገሮች የሚኖሩት ናቸው። በ2012 (እ.ኤ.አ ) በዓለም ላይ ተጠቂ ለሆኑ ብዙዎቹ ሴቶች በምክንያትነት በጥናቶች የጠቀሱትም ዝቅተኛ ግንዛቤ ያላቸው ሴቶች መብዛት ፣ ወደ ህክምና ተቋማት ያለመሄድ ፣ የፋይናንስ እጥረትና የአገልግሎት አለመዳረስ እንዲሁም የብሄራዊ ካንሰር ምዝገባና ክትትል እጥረት እንደሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ። በሀገራችንም ከ21 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ 15 ዓመትና ከዚያ በላይ የሆናቸው ሴቶች ጉዳዩ የሚመለከታቸው ይሆናል።

የመገናኛ ብዙሃን ሙያተኞች ካንሰር ፎረም ሊቀመንበር የኢትዮጵያን ሄራልድ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የሆኑት አቶ ዳኜ ቢያዝን በበኩላቸው «እንዲህ አይነት ያልተነገረላቸው ገዳይ በሽታዎች በተለይ በሀገራችን ሴቶች ላይ የሚያደርሱት ጉዳት ከፍተኛ ስለሆነ መገናኛ ብዙሃን አቅማች በፈቀደው ሁሉ የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራው ላይ መረባረብ አለብን» ብለዋል። ከዚህ አንፃር የመገናኛ ብዙሃን ፎረሙ ቀስ በቀስ ሁሉንም የሚዲያ አካላት እያካተተ፣ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሪትና ፓስፋይንደርን የመሰሉ ድጋፍ ሰጪዎችን እገዛ ተጠቅሞ ለተሻለ ውጤት እንደሚንቀሳቅስ ነው የጠቆሙት።

የካንሰር መነሻ ምክንያቶች፣ ምልክቶችና መከላከያ መንገዶችንም ሆነ የማህፀን በር ጫፍ ካንሰርን መረጃዎች ከህክምና ሙያተኞቹና ከሚኒስቴሩ የኤሌክትሮኒክስ የመረጃ ባንክና ህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት እንድናገኝ ሊመቻችልን ይገባል ያሉት ሰብሳቢው ፤ ሙያተኞች እጃችን ላይ ባሉ የህትመትና ኤሌክትሮኒክ መገናኛ ብዙሃን ብቻ ሣይሆን በማህበራዊ ድረ ገፆች ፣ በአነስተኛ «ኪቶችና » ብሮሸሮች ጭምር መረጃዎችን በማሰራጨት ዜጎችን መታደግ ይገባናል ነው ያሉት።

የማህፀን በር ካንሰርን ብቻ ሳይሆን የካንሰር በሸታ በሀገሪቱ ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት ለመቀነስ አስፈላጊውን እናደርጋለን ያሉ ሌሎች የፎረሙ አባላትም ከተባባሪ አካላት ጋር ተቀናጅተው ለመስራት ቆርጠው ተነስተዋል። ለዚህም ሲባል ከዚህ ቀደም ብልጭ ብለው ከጠፉ የተለያዩ ፎረሞችና የመገናኛ ብዙኃን ማህበራት አደረጃጀቶች ትምህርት መውሰድ እንደሚገባም አውስተ ዋል።

ትልቁ እርምጃ ህዝቡን ያሳተፈ የኮሙኒ ኬሽንና ሚዲያ ስራ መስራት እንደሆነም ፎረሙ እንዲጠናከር እገዛ እያደረጉ ያሉት የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት ተወካይ አቶ ታደገ ገልፀዋል። በተለይ ብዙም ግልፅነት ያልተፈጠረበትን የማህፀን በር ካንሰር መንስዔ፣ መተላለፊያ መንገዶችን በማሳወቅ፣ የህክምናውን ቀላልነት በማስገንዘብ ሴቶች ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን እንዲታደጉ ማድረግ ወቅቱ የሚጠይቀው ሥራ ነው ብለዋል።

ሲጠቃለል የእናቶችን ህልፈት ለመታደግ እንደ አንድ ቁልፍ ተግባር የሚቆጠረው የማህፀን በር ጫፍ ካንሰርን የመከላከል ጉዳይ በጋራ እንተግብር የሚል መልዕክት መሰንዘር እንወዳለን። ይህ መረጃ የደረሳችሁ ሁላችሁም (ያነበባችሁት) ወንዶችም ሚስቶቻችሁን፣ እናት፣ እህትና ልጆቻችሁን ወደ ህክምና ተቋማት በመውሰድ ማስመርመር ይኖርባች ኋል። በየትኛውም የስራ ደረጃ ላይ ያላችሁ ሴቶችም ለራሳችሁ እወቁበት እንላለን።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment