Thursday, August 28, 2014

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት አያያዝ የውጪ ባለሃብቶችን እየጋበዘ ነው

(Aug, 28, 2014,(አዲስ አበባ))--ያለፉት ጥቂት ዓመታት በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የታየው የኢኮኖሚ ዕድገት ለታዳጊ አገራት ተምሳሌት ተደርጎ የሚጠቀስ ነው። ለውጡ አንቀላፍታበት ከነበረው ረጅም ዘመን ጋር ሲነጻጸር ልዩነቱ የሰማይና የምድር ያህል ነው፤ ከጉዞ በላይ እርምጃ፤ ከእርምጃም በላይ ሩጫ ላይ ናት ሲሉ ብዙዎች አድንቀዋታል።

በእርግጥም አገር ውስጥ ላለነው ኢትዮጵያውያን ይህን ሁኔታ ለመረዳት የሩቅ ታዛቢ ምስክር አያሻንም። ይሁንና በተጨባጭ በአገሪቱ የሚታዩ ለውጦች ከውስጥ አልፎ የውጪው ማህበረሰብ ያለማመንታት ስለ ልማቷ እንዲናገር፤ ስለ ዕድገቷም እንዲያወራ አስገድደውታል።

ቀደም ሲል በጥቂት ከተሞችና አካባቢዎች ብቻ ተወስኖ የቆየው የመሰረተ ልማት አቅርቦት ዛሬ በመላው አገሪቱ እየተስፋፋ ይገኛል። የአንድ አገር የመሰረተ ልማት አቅርቦት በተስፋፋና ዕድገት ባመጣ ቁጥር ደግሞ በዚያው ልክ የሰብአዊ መብት አያያዝም እየዳበረ እንደሚሄድ ይታመናል። ይህ በኢትዮጵያ በተግባር እየታየ መምጣቱን የዘርፉ ምሁራን ያረጋግጣሉ።

ባለፉት ዓመታት በኢትዮጵያ በሁሉም አቅጣጫ በተዘረጋው መሰረተ ልማት፣ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ፣ ፈጣን ምጣኔ ሃብታዊ ዕድገትና የአገሪቱ የሰብዓዊ መብት አያያዝ በእጅጉ ተሻሽሏል። በቅርቡ በጄኔቭ ስዊዘርላንድ በተካሄደው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ምክር ቤት ጉባኤም ኢትዮጵያ በሰብአዊ መብት አያያዝ የተሻለ ደረጃ ላይ መድረሷን ነው አብዛኞቹ የምክር ቤቱ አባላት የመሰከሩት።

የመንግስታቱ ድርጅት አባል አገራት በየአምስት ዓመቱ የሰብአዊ መብት አያያዛቸውን የተመለከተ ሪፖርት ለምክር ቤቱ ያቀርባሉ። ኢትዮጵያ የመጀመሪያ ሪፖርቷን በ2001 ዓ.ም ለምክር ቤቱ ስታቀርብ ቢጨመሩና ቢስተካከሉ በሚል 96 ምክረ ሃሳቦች ከአባላቱ ተለግሰዋት ነበር።

አገሪቱም ለዘንድሮው ሪፖርት በተሻለ መልኩ ለመቅረብ ብቻ ሳይሆን የዜጎቿን የአኗኗር ሁኔታ ለማሻሻልም የቤት ስራዋን በትጋት ስትከውን ቆይታለች። ጊዜው ደርሶ የዘንድሮውን ሪፖርት ለማቅረብ ወደ ጄኔቭ ስዊዘርላንድ ያቀናው በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርሃነ ገብረክርስቶስ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን በእርግጥም የቤት ስራው በተገቢው መንገድ ስለመፈጸሙ ዕውቅና የሚሰጥ ግብረ መልስ ከምክር ቤቱ አባላት ይዞ ተመልሷል።

ቡድኑ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በተጨማሪ ከመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት፣ ከፍትህ፣ ከፌዴራል ጉዳዮች፣ ከሴቶች፣ ህጻናትና ወጣቶች ጉዳይ ሚኒስቴርና ከኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን የተወጣጡ አባላትን የያዘ ነበር።

ከምክር ቤቱ አባል አገራት ተወካዮች አብዛኞች ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊና ትክክለኛ መረጃ የነበራቸው ቢሆንም የልዑካን ቡድኑ የአገሪቱን የአምስት ዓመታት የስራ ውጤት ለምክር ቤቱ አቅርቧል፣ ጥያቄና አስተያየቶችን ተቀብሎም ማብራሪያ ሰጥቷል። 119 አገራት ቢጨመር፣ ቢስተካከልና ቢቀየር ያሉትን ሃሳብም ሰነዘሩ።

ከተሰነዘሩት 252 ምክረ ሃሳቦች መካከል 181ዱ የአገሪቱን የልማት፣ የዴሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ግንባታ ሊደግፉ የሚችሉ በመሆናቸው በኢትዮጵያ መንግስት ልዑካን በኩል ሙሉ ተቀባይነትን አግኝተዋል።

ከምክረ ሃሳቦቹ 18ቱ ደግሞ ወዲያውኑ ውሳኔ የሚሰጥባቸው አልነበሩም። ምክክር የሚያሻቸው ነበሩና ጊዜ ወስደን እንምከርባቸው በሚል ልዑካኑ ወደ አገር ቤት ይዘዋቸው ተመልሰዋል።

ምንም እንኳን አብዛኞቹ ከምክር ቤቱ አባላት ለኢትዮጵያ የተሰጡ ሃሳቦች አዎንታዊ ድጋፍን ያዘሉ ቢሆኑም በጀመረችው የዕድገት ጉዞ ላይ ምንም የማይጨምሩ፤ ይልቁንም እየሄደችበት ካለው አቅጣጫና ፖሊሲ ጋር ተቃርኖ ያላቸው ጥቂት አስተያየቶችም ተሰንዝረዋል።

«የጸረ ሽብር ህጉንና የበጎ አድራጎት ማህበራት ማቋቋሚያ አዋጅን ሰርዙ» የሚሉት ከነዚህ ጥቂት ሃሳብና አስተያየቶች መካከል የሚጠቀሱና በኢትዮጵያ በኩል ተቀባይነትን ያላገኙ ናቸው።

የዜጎችና የአገር ደህንነትን ለመጠበቅ ተግባራዊ የተደረገው የጸረ-ሽብር ህጉ በሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚያስከትለው ተጽዕኖ እንደሌለ፣ የበጎ አድራጎት ማህበራት አዋጅም ቢሆን ህግና ደንብን አክብረው ለሚሰሩት እንቅፋት ያለመሆኑን የቡድኑ አባላት ለምክር ቤቱ አስረድተዋል።

የተለያዩ የዓለም አገራትን አቅፎ በያዘው ምክር ቤት ኢትዮጵያ ያገኘችው ተቀባይነት ለቀጣይ ስራዋ አበረታችና የሰብአዊ መብትን ለማስከበር የሄደችባቸውን ርቀቶች የሚያሳይ ነበር። አገሪቱ ሰብአዊ መብትን በማስከበሩ ሂደት የጎረቤት አገራት ስደተኞችን ጭምር ተቀብላ በማስተናገድ እየተወጣች ያለችው ኃላፊነት በዓለም አገራትና በመንግስታቱ ድርጅት ዘንድ አስመስግኗታል።

በአሁኑ ወቅት 600 ሺ የሚሆኑ የተለያዩ አገራት ስደተኞች በኢትዮጵያ ይገኛሉ፤ እነዚህ ስደተኞች ከሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን፣ ከሶማሊያ፣ ከኤርትራና ከሌሎችም የአፍሪካ አገራት የመጡ ናቸው።

ስደተኞችን ተቀብሎ ማስተናገድ በበለፀጉት አገራት ኃላፊነትን ከመወጣት በዘለለ እንደ ግዴታም የሚታይ ተግባር ሊሆን ይችላል። ኢትዮጵያን በመሳሰሉና የምጣኔ ኃብት ደረጃቸው ዝቅተኛ በሆኑ አገራት ሲከወን ግን ከግዴታነት ይልቅ አገራቱ ሰብአዊ መብትን ለመጠበቅ እየሄዱበት ያለውን ርቀትና ቁርጠኝነታቸውን የሚያሳይ ይሆናል።

ለዚህም ይመስላል የመንግስታቱ ድርጅት ለአገሪቱ ከሰጠው እውቅና ባሻገር እያከናወነች ባለችው የጎረቤት ስደተኞችን የመርዳት ተግባር የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እገዛ ያሻታል እያለ የሚገኘው።

ሰብአዊ መብት ለተወሰነ አካል፣ በጾታ፣ በሃብት፣ በቋንቋና ብሄር፣ በዜግነት፣ በቀለም አልያም በኃይማኖት የሚለገስ ስጦታ ሳይሆን የሰው ልጅ በሰውነቱ የሚያገኘውና ሊሟላለት የሚገባ መሰረታዊ መብት ነው። የኢትዮጵያ የዕድገት ግስጋሴ በአንድም በሌላም መንገድ ዜጎች ሰላም እንዲያገኙ፣ አኗኗሯቸው እንዲሻሻልና የሰብአዊ መብታቸው እንዲረጋገጥ እያደረገ ይገኛል።

«አገሪቱ ያጸደቀቻቸውን አለም አቀፋዊና አህጉራዊ የሰብአዊ መብት ሰነዶችና ስምምነቶች ከማስፈጸም ባሻገር ሰብአዊ መብትን ማስከበር የልማት አንዱ አካል ነው» በማለት የአምስት ዓመታት የሰብአዊ መብት የድርጊት መርሃ ግብር ቀርጻ ወደ ስራ መግባቷ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ምክር ቤት አባላት አስመስግኗታል።

የድርጊት መርሃግብሩ የሲቪል እና የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊና የባህል መብቶች፣ ለመብት ጥሰት ተጋላጭ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች መብት እና የአካባቢ ደህንነትና የልማት መብቶች በሚል ተከፍለው የሚከወኑ ርዕሰ ጉዳዮችን በውስጡ ይዟል።

« መንግስት የተሟላ የዴሞክራሲ ስርዓት ለመገንባት ቁርጠኛ አቋም መያዙ፣ በሂደቱም ህዝቡ ከፍተኛ ተሳትፎ ማድረጉና ለሂደቱ የሚያስፈልጉ ተቋማት መመስረታቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ ለሰብዓዊ መብት መሻሻል ምክንያት ሆነዋል» ሲሉ የልዑካን ቡድኑ መሪ አምባሳደር ብርሃነ ገብረክርስቶስ ይናገራሉ።

የፍትህ ስርዓቱም የተሟላ ደረጃ ላይ ደርሷል ባይባልም በየጊዜው መሻሻል እያሳየ መጥቷል። ቀደም ሲል በችግርነት ይነሱ የነበሩት የሴት ልጅ ግርዛትና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች መቀነስም የተመዘገበው ለውጥ አካል ሆነዋል።

በአብዛኛው የምክር ቤቱ አባላት ዘንድ የተገኘው «ኢትዮጵያ ሰርታለች፤ ለውጥም አምጥታለች» የሚል ምስክርነት ለአገሪቱ በጎ ገጽታና የውጭ ጎብኚና ኢንቨስትመንት ለመሳብ ካለው ጠቀሜታ ባሻገር በየአጋጣሚው የአገሪቱን ስም የማጥፋት ዘመቻ ለሚከፍቱ አካላት አስደንጋጭ ነበር።

በተለይም እንደ አምነስቲ ኢንተርናሽናልና ሂዩማን ራይትስ ዎች የመሳሰሉ ገለልተኝነታቸው አጠያያቂ የሆነ «የሰብአዊ መብት ተሟጋች ነን» የሚሉ አካላት በየጊዜው ሚዛናዊ ያልሆነ ሪፖርት በማውጣት የኢትዮጵያን የሰብአዊ መብት አያያዝ ጥላሸት ለመቀባት የሚያደ ርጉትን ሙከራ ውድቅ የሚያደርግና የተቋማቱ ጥያቄ በትክክልም የሰብአዊ መብት ያለመሆኑን በግልጽ ያሳየ ነው ተብሏል።

ኢትዮጵያ እየሄደችበት ላለው የልማት ጉዞ እንቅፋት ሊሆኑ ይችላሉ ከተባሉ ስጋቶች ባሻገር የተጀመረውን ስራ የሚያሞግሱና ለቀጣዩ የአምስት ዓመታት ሪፖርት ግብአት የሚሆኑ የተለያዩ ሃሳቦች በምክር ቤቱ አባላት በየተራ ተነስተዋል።

በኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ግንባታ መሰረቱ ተጣለ እንጂ ሙሉ በሙሉ አልተጠ ናቀቀም፤ በርካታ መሰራት ያለባቸው ተግባራት በጅምር ላይ ናቸው። ይሁንና ዛሬ በጽኑ መሰረት ላይ ከታነጸ የነገን ስራ በእጅጉ እንደሚያቀለው ይታመናል።

በብዙሃኑ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አባል አገራት ኢትዮጵያ ያገኘችው ተቀባይነት ደግሞ ግስጋሴዋን ይበልጥ ለማሳመር ስንቅ ይሆናል፣ ድጋፍ ላለመስጠት የታጠፉ ጥቂት እጆችም በቀጣዩ ሪፖርት እንደሚዘረጉ አንጠራጠርም በማለት የልዑካን ቡድኑ አባላት በእርግጠኝነት ተናግረዋል።

ምክር ቤቱ ለኢትዮጵያ የሰጠው ምስክርነት ነገ የበለጠ ስራ እንዲከናወን መንገድ የሚጠርግ ነው። ምስክርነቱ በመንግስታት የተሰጠ መሆኑም ትልቅ ትርጉም የሚሰጠው ነው። ይህ ደግሞ ስለ ኢትዮጵያ መልካም ማውራት የማይወዱትን ጭምር ሳይወዱ በግድ ነገ ስለ አገሪቱ እውነታውን እንዲናገሩ ያስገድዳቸዋል፤ «ያሻንን እንናገር» ቢሉ የሚቀበላቸው አይኖርምና።
ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ, አዲስ አበባ

No comments:

Post a Comment