Friday, March 21, 2014

ኢትዮጵያ ግድቡን በተመለከተ «ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለማሳወቅ የራሷን ስትራቴጂ ትከተላለች» -አምባሳደር ዲና ሙፍቲ

(Mar 20, 2014, (አዲስ አበባ))--ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በተመለከተ «ኢትዮጵያ ያለውን ተጨባጭ እውነታ ለዜጎቿም ሆነ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የምታሳውቅበት የራሷን ስትራቴጂ ትከተላለች» ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አስታወቁ።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ የአገሪቱን ወቅታዊ ጉዳይ አስመልክተው፤ ትናንት በሰጡት መግለጫ እንደተናገሩት፤ ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በተመለከተ ለሚነሱ ጉዳዮች ሁሉ የራሷን ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ መስመር ይዛና በትክክለኛ መረጃ ላይ ተመስርታ የማሳወቅ ሥራን እንጂ፤ ግብጻውያኑ የሚያራግቡትን የሐሰት ፕሮፓጋንዳ ተከትላ የምታከናውነው አንዳችም ነገር አይኖርም።

«ግብጻውያን ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለአገር ውስጥ የፖለቲካ ፍጆታ እያዋሉት ነው» ያሉት አምባሳደር ዲና፤ ይህ አጀንዳቸው በአገር ውስጥ ያለውን የፖለቲካ ውጥረት በጊዜያዊነት ለማርገብ እየተጠቀሙበት መሆኑን ተናግረዋል። ለእዚህም በኢትዮጵያ በኩል ግድቡ ለግብጽ ጥቅም እንጂ ጉዳት የሌለው መሆኑን ለግብጽ ሕዝብና ለወዳጆቿ የመግለጹ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ የግብጻውያኑን የሐሰት ፕሮፓጋንዳ እግር በእግር ተከታትሎ መልስ የመስጠት አሰራር እንደማትከተል ጠቁመው፤ ለዓመታት የማይዛነፈውን መርህ በመከተል የልማት ሥራዋን እንደምታከናውን እንጂ ግብጽን ወይም ሌሎች የተፋሰሱን አገሮች የሚጎዳ ሥራ እንደማትሠራ የማሳወቅ ተግባር ላይ እንደምታተኩር አብራርተዋል።

እንደ አምባሳደር ዲና ገለጻ፤ ግብጽ የሐሰት አጀንዳዋን ለማሳካት ስትል የማይጨበጡና ተቀባይነት የሌላቸው ፕሮፓጋንዳዎችን እየተጠቀመች ትገኛለች። የኢትዮጵያን ልማት ከማይፈልጉ እንደ ኤርትራ ካሉ አገሮች ጋርም በመወዳጀት ፍላጎቷን ለማሳካት ማሰቧም አልቀርም። ሆኖም በኢትዮጵያ በኩል እየተከናወነ ያለው ሥራ በአፍራሽ ሃሳባቸው ተገፋፍቶ ወደሌላ እርምጃ የመሄድ ሳይሆን ጉዳዩን የመከታተልና ትክክለኛውን መርህ መሠረት በማድረግ ለሁሉም ግንዛቤ የመፍጠር ነው።

ኢትዮጵያ እያከናወነች ባለው ያላሰለሰ ጥረትም በተፈጠረው ግንዛቤ በውጭ ካሉ ኢትዮጵያውያን በተጨማሪ፤ በርካታ ሱዳናውያን እንዲሁም በካርቱም የሚኖሩ ግብጻውያን ለህዳሴው ግድብ ግንባታ የሚውል የቦንድ ግዢ እየፈጸሙና አስተዋጽዖ እያደረጉ መሆናቸውን አምባሳደሩ ጠቁመዋል።

ከዚህ ጋር በተያያዘም በቅርቡ የኬንያው ፕሬዚዳንት በኢትዮጵያ ባደረጉት ይፋዊ የሥራ ጉብኝት በተደረገው ሰፊ ውይይት በድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ላይ ሁለቱ አገሮች በጋራ ተጠቃሚ በሚሆኑበትና በሚያለሙበት ጉዳይ ላይ ተስማምተዋል። የናይል ተፋሰስ ልማት የትብብር ስምምነት ማዕቀፍን በተመለከተም በኬንያ በኩል በሦስት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ለፓርላማ ቀርቦ እንደሚጸድቅ መግባባት ላይ ተደርሷል።

በጉብኝቱ በተለይ በኢትዮጵያና ኬንያ መካከል እ.ኤ.አ በ2012የተፈረመውን የስፔሻል ስታተስ ስምምነት የማጠናከር፤ይህንንም በንግድና ኢንቨስትመንት ወደላቀ ደረጃ ለማድረስና የጋራ የቴክኒክ ኮሚቴ ለመመስረት ተወስኗል። በሁለቱ አገሮች መካከል ያለው ጠንካራ የድንበር ጥበቃ ተጠናክሮ በሚቀጥልበት ሁኔታ ላይም በመወያየት የጋራ መግባባት ተፈጥሯል።

በሌላ በኩል በመግለጫው እንደተ ጠቆመው፤ የ25ኛው የኢጋድ የመሪዎች ጉባኤም ሆነ 51ኛው አስቸኳይ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ስብሰባ በተሳካ ሁኔታ ተከናውኗል። መሪዎቹም በስብሰባቸው በደቡብ ሱዳን ሰላም ለማስፈን አስተዋጽኦ ያበረከቱ አካላትን ያመሰገኑ ሲሆን፤ በቀጣይም ይኸው ተግባር በሰብዓዊ መብት ጥበቃም ሆነ በሌሎች ድጋፎች ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል። አባል አገሮቹም የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡ ተወስኗል። በተመሳሳይም በሶማሊያ ያለውን ጉዳይ የተመለከተውና ለፌዴራል መንግሥቱ ድጋፍ በሚሰጥበት ሂደት ላይ ምክክር ተደርጓል፤ አቅጣጫም ተቀምጧል።
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment