Monday, March 10, 2014

ግብፃውያን ሆይ ወደ ቀልባችሁ ተመለሱ! (ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ)

(Mar 10, 2014, (አዲስ አበባ))--ግብፅ በራሷ ፍቃድ አቋርጣው ወደነበረው ድርድር ለመመለስ ጥሪ ማቅረቧን በሰማን በቀናት ውስጥ ቀደም ሲል ከድርድሩ ራሷን ካወጣችበት የተለየ አቋም ይዛ ባለመቅረቧ የቅርብ ጊዜ ውይይቱም ያለ ፍሬ መበተኑን ሰምተናል፡፡ የግብፅ የመስኖና የውሃ ሚኒስትር መሐመድ አብዱል ሙጣሊብ ስልክ ደውለው ወደ አዲስ አበባ መጥተው በግንባታ ላይ ባለው የህዳሴ ግድብ ላይ ለመወያየት ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት ነበር ወደ ኢትዮጵያ የመጡት፡፡

ይሁን እንጂ ቀደም ሲል አገራቸው ይዛ የነበረውን የዓለም አቀፍ ባለሙያዎች ቡድን ተጨማሪ ጥናት እንዲያከናውን የሚጠይቅ፣ እንዲሁም «በግንባታው ላይ መተማመንን ማጐልበት» የሚል እ .አ. አ በ1959 ዓ.ም አገኘሁት የምትለው የውሃ ድርሻ እውቅና እንዲሰጥ የሚጠይቅ አቋሞች ይዘው በመቅረባቸው ከሦስት ሰዓት ቆይታ በኋላ ውይይቱ መቋረጡን የኢትዮጵያ የውሃ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትር አቶ አለማየሁ ተገኑ ተናግረዋል፡፡

የግብፁ የውሃና የመስኖ ሚኒስትር ምንም አዲስ ነገር ሳይዙ አዲስ አበባ ደርሰው ወደአገራቸው እንደተመለሱ መግለጫ መስጠታቸውንም ሰምተናል፡፡ በመግለጫቸው ከኢትዮጵያ ጋር መደራደር እንደበቃቸውና ሌሎች አማራጮችን ለመውሰድ ፍላጎት እንዳላቸው አስታውቀዋል፤ ሌሎቹ አማራጮች ምን እንደሆኑ ግን አልተናገሩም፡፡ ከዚሁ ጋር አያይዘው «በህዳሴው ግድብ ዙሪያ በኢትዮጵያና በግብፅ መንግሥታት ዙሪያ የተፈጠረውን አለመግባባት ለማጥበብ በግብፅ በኩል የሚደረጉ ጥረቶችን ኢትዮጵያ እያደናቀፈች ነው» ማለታቸውንም ሰምተናል፡፡

ምንም እንኳን ከዚያ ወዲህ ባሉት ቀናት ሚዛናዊ የሆኑ ምሁራኖቻቸው ጉዳይ በቴክኒክ ፋይዳ ማየት ከፖለቲካ ዋጋ በላይ መሆኑን እየመከሩ ቢሆኑም የናይል ውሃ ብቸኛ የግብፅ የተፈጥሮ ሀብት አይደለም፡፡ ወደሱዳንና ግብፅ የሚፈሰው የናይል ወንዝ የውሃ ምንጭ የሆኑትና ወንዙ ድንበራቸውን አቋርጦ የሚወጣባቸው አስር ያህል የተፋሰሱ ሀገራት በመርህ ደረጃ የተፈጥሮ ሀብቱ ተጋሪ ባለቤቶች ናቸው፡፡ ከዚህ የባለቤትነት መብታቸው የሚመነጭ በውሃው የመጠቀም መብትም አላቸው፡፡ ይሁን እንጂ እንደማንኛውም የጋራ ሃብት አንዱ ሌላው ላይ የጎላ ጉዳት የማያስከትልበት ፍትሐዊ የውሃ አጠቃቀም ሊኖር ይገባል፡፡ በዚህ መነሻነት ከናይል ተፋሰስ አገራት መካከል ስድስቱ ወደ ፍትሐዊ የውሃ አጠቃቀም የሚወስዳቸውን የስምምነት ማዕቀፍ ተፈራርመዋል።

ግብፅ ይህን ወደፍትሐዊ የውሃ አጠቃቀም የሚወሰደውን የስምምነት ማዕቀፍ አልተቀበለችውም፡፡ ኢትዮጵያ ታላቁን የህዳሴ ግድብ ለመገንባት ስትነሳ ይህን የስምምነት ማዕቀፍ መነሻ አድርጋ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ማስገንባት የጀመረችው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሊያስከትል በሚችለው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተፅእኖ ዙሪያ በባለሞያ ቡድን የቀረበው ምክረሃሳብ የሚደረገውን ውይይት የማይረባ ምክንያት በማቅረብ የምታደናቅፈው በአጠቃላይ የተፋሰሱን ሀገራት ፍትሐዊ የውሃ ተጠቃሚነት መብት ስለማትቀበል ነው፡፡

በ1959 ዓ.ም የሌሎቹን የናይል የውሃ ምንጭ የሆኑትን የተፋሰሱን ሀገራት ሳያካትት ግብፅና ሱዳንን ብቻ የናይል ውሃ ባለድርሻ ያደረገውን፣ በተለይ ግብፅን የአንበሳ ድርሻ ባለቤት ያደረጋትን ተገቢ ያልሆነ ስምምነት እንዲከበር የሚጠይቀውን «በግንባታው ላይ መተማመንን ማጐልበት» የሚል ሃሳብ ማቅረቧ ይህን በግልፅ ያረጋግጣል፡፡ የህዳሴ ግድብ ሊያሳድረው የሚችለውን ተፅእኖ የሚያጠና ሌላ ቡድን ይቋቋም የሚለውን ሃሳብ ያቀረበችውም የግድቡ ግንባታ ሥራ እንዲጓተት ምክንያት ፍለጋ እንጂ ጥናቱ ችግር አለበት ብላ ስለምታምን አይደለም፡፡ ጥናት አድራጊው ቡድን መቋቋሙን ተስማምታበት ነበር። ቡድኑ ያቀረበውንም ሪፖርት ተቀብላ ነበር፡፡ መንሸራተቱ የመጣው መጨረሻ ላይ ነው፡፡

_እንደሚታወቀው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እንደተጀመረ ግድቡ በታችኛው የተፋሰሱ ሀገራት ላይ ሊያደርስ የሚችለውን ተፅእኖ የሚያጠና ዓለም አቀፍ የባለሙያዎች ቡድን ሲቋቋም፣ ግብፅ ከኢትዮጵያና ከሱዳን ጋር ተስማምታ ፊርማዋን አኑራለች። የባለሙያዎቹ ቡድን ውስጥም ሁለት ባለሙያዎችን ወክላለች፡፡ በዚህ አኳኋን የተመሰረተው አጥኚ ቡድን ከኢትዮጵያ፣ ግብፅና ሱዳን ከእያንዳንዳቸው የተወከሉ ሁለት ሁለት አባላትን፣ እንዲሁም ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ዓለም አቀፍ ተቋማት የተወከሉ አራት አባላት በድምሩ አስር አባላት ይዞ ነበር ሥራውን የጀመረው፡፡ ይህ ቡድን ጥናቱን አጠናቅቆ ባለፈው ዓመት ማገባደጃ - ሰኔ፣ 2006 ዓ.ም ላይ ሪፖርቱን ይፋ አድርጓል፡፡

በእዚህ ሪፖርት መሠረት ታላቁ የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ የህዳሴ ግድብ ወደ ሱዳንና ግብፅ የሚፈሰው የናይል ውሃ ላይ ምንም ተፅእኖ እንደማይኖረው፣ እንዲሁም ግድቡ በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ባላቸው የግንባታ ተቋራጮችና የምህንድስና አማካሪዎች የሚሰራ በመሆኑ ምንም ዓይነት የቴክኒክ ችግር እንደማይኖረው አረጋግጠዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የግደቡ ግንባታ በታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎች ላይ ሊያደርስ የሚችለውን ተፅእኖ ሙሉ በሙሉ ለማስቀረት ተግባራዊ መሆን አለባቸው ያላቸውን ምክረ ሃሳቦች (recommendations) አቅርቧል፡፡

አሁን በሦስቱ አገራት መካከል ውይይት ያስፈለገው ይህ ተስማምተው ያቋቋሙት የባለሙያዎች ቡድን ያቀረባቸውን ምክረሃሳቦች ተግባራዊ ለማደረግ ነው፡፡ በዚህ ዙሪያ መግባባት ላይ ለመድረስ ከዚህ ቀደም ሦስት ጊዜ ውይይቶች ተደርገዋል፡፡ በእነዚህ ውይይቶች ላይ ምክረ ሃሳቡን ተግባራዊ የሚያደርግ ከሦስቱም ሀገራት የተውጣጣ የባለሙያዎች ቡድን የማቋቋም ጉዳይ ዋናው አጀንዳ ነበር፡፡

ይሁን እንጂ ግብፅ ይህን ከመቀበል ይልቅ ከላይ የተገለፀውን «ጥናቱ በሌላ አጥኚ ቡድን እንደገና ይጠና» የሚል ጎታች ሃሳብ አቅርባለች፡፡ ከዚሁ ጋር «በግንባታው ላይ መተማመንን ማጐልበት» የተሰኘ እ.አ.አ በ1959 ዓ.ም ሌሎቹን የተፋሰሱን አገራት ሳይጨምር አገኘሁት የምትለውን የውሃ ድርሻ እንዳይነካ የሚጠይቅ ሃሳብ አቅርባ ይህ በኢትዮጵያና ሱዳን ተቀባይነት በማጣቱ ግብፅ ድርድሩ እንዳይቀጠል አንቃ ይዛዋለች፡፡ እንግዲህ ይህንኑ ድርድሩን የሚያንቅ አሮጌ አቋማቸውን ይዘው መጥተው ያለውጤት ወደሀገራቸው የተመለሱት መሐመድ አበዱል ሙጣሊብ «ድርድሩ አብቅቶለታል፣ ካሁን በኋላ ወደሌሎች አማራጮች ነው የምንሄደው» በሚል የሰጡት መግለጫ ምንም አዲስ ነገር የለውም፡፡ በድርድሩ ላይ የያዟቸው አቋሞች ይህንኑ የሚያመላክቱ ነበሩ፡፡ ከአንድ ወር በፊት ድርድሩን ጥለው ሲወጡም ይህንኑ ነበር የገለፁት፡፡

ግብፅ ከአንድ ወር በፊት ድርድሩን አንቃ እንዳይቀጥል ካደረገች በኋላ ባለሥልጣኖቿ የገለጿቸው አቋሞች ሌሎች አማራጮችን ለመያዝ መወሰኗን የሚያመለክቱና በሀገራቱ መካከል ውይይቱ እንዲቀጥል ማድረግንና በትብብር የመስራትን አካሄድ የሚጎዱ ነበሩ። ከወደ ግብፅ የተሰማው መግለጫ ወደ ድርድር ከመሄድ ይልቅ «ጉዳዩን ወደተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት እንወስደዋለን፣ ለዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት እናቀርበዋለን» የሚል ነበር። በእነዚህና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሰፋ ያለ ማብራሪያ ስለተሰጠበት መደጋገሙ የሚያሰለች ቢመስልም ከሳምንታት በፊት የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ የሰጡትን ምላሽ መጥቀስ ተገቢ ሆኖ አግኝቼዋለሁ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታን በተመለከተ ኢትዮጵያ ግብፅና ሱዳን የሦስትዮሽ የጋራ ምክክር ከጀመሩ ሁለት ዓመት ከመንፈቅ እንደሆነ በመግለፅ ነበር ጉዳዩን ማብራራት የጀመሩት፡፡ ኢትዮጵያ «የግድቡ ግንባታ የታችኞቹ ተፋሰስ አገራት ላይ ሊያስከትል የሚችለው ተፅዕኖ ካለ ማጥናት ይገባል»፣ የሚል አቋም ይዛ ጥናቱ እንዲካሄድ በቀዳሚነት አቋም መያዟንና፣ በዚህ የኢትዮጵያ መንግሥት አቋም ላይ በመመስረት የባለሙያዎች ቡድን ተቋቁሞ ጥናት መጀመራቸውን አስታወሰው በጉዳዩ ዙሪያ የሚከተለውን ማብራሪያ ሰጥተዋል።

ግድቡን በተመለከተ አለመግባባቶች ካሉ በውይይትና በመቀራረብ ለመፍታት በኢትዮጵያ መንግሥት በኩል ካለው ፅኑ እምነት በመነሳት ውይይቶች ተደርገዋል፡፡ በዚህም መሠረት ከጊዜ ወደ ጊዜ በተወሰኑ ጉዳዮች ላይ መግባባት ተችሏል፡፡ በተለይም የሱዳን መንግሥትና የኢትዮጵያ አቋም አንድ እንዲሆን ማድረግ ተችሏል፡፡ ይህ የሚያሳየው የያዝነው አቋምና መንገድ የትብብር መሆኑን ነው፡፡ ነገር ግን በግብፅ በኩል ለትብብርና ለጋራ ተጠቃሚነት እንዲሁም ዕድገት ያላቸው አመለካከት የተለያየ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ የታላቁ ህዳሴ ግድብን በተመለከተ በዓለም አቀፍ የባለሙያዎች ቡድን ተፅዕኖው እንዲጠና ከተደረገ በኋላ የባለሙያዎች ቡድን ባቀረበው ምክረ ሃሳብ ላይ ተመሥርተን ወደፊት መጓዝ አለብን የሚል አቋም ይዘናል፡፡ ግብፆች ደግሞ ይህ መሆን የለበትም በማለት እንደገና ዓለም አቀፍ የባለሙያዎች ቡድን ተቋቁሞ ጥናቱን ከዜሮ ማካሄድ አለብን የሚል ጥያቄ አቅርበዋል፡፡

ይህ በየትኛውም መንገድ ተቀባይነት የለውም፡፡ ምክንያቱም ተስማምተውና ተፈራርመው የመሠረቱት የባለሙያዎች ቡድን ሪፖርቱን ለሦስቱም መንግሥታት አቅርቧል፤ በድጋሚ ከዜሮ የምንጀምርበት ምክንያት የለም፡፡ በመሆኑም ግብፅ ብቻዋን ኢትዮጵያና ሱዳን ደግሞ ተመሳሳይ አቋም በመያዛቸው ምክንያት ለሚቀጥለው ጊዜ አስበውበት እንዲመጡ በሚል ውይይቱ ለጊዜው ተቋርጧል፡፡ እንደሚታወቀው ድርድር በአንድ ጊዜ ተጀምሮ የሚያበቃ ጉዳይ አይደለም፡፡ በእኛ እምነት ድርድሩ አበቃ ብለን አናምንም።  (ይቀጥላል)
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment