Friday, February 28, 2014

ታላቁ የህዳሴ ግድብ-ታላቅነቱ ለአፍሪካም ነው!

(Feb 28, (አዲስ አበባ))--የኢፌዴሪ መንግሥት የሀገሪቱን የተፈጥሮ ሀብት! ሰፊ የሕዝብ ጉልበትና ዕውቀት እንዲሁም ሀገራዊ ምቹ ሁኔታዎች ያገናዘቡ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ነድፏል፡፡ የልማት፣ የመልካም አስተዳደርና የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ የፖሊሲ አቅጣጫዎቹ ተቀርጸው ምልዐተ ሕዝቡ የጋራ ግንዛቤ ከጨበጠባቸው ወዲህ ባሉት አስራ አንድ የትግበራ ዓመታትም ያልተቋረጠ ባለ ሁለት አሃዝ ሀገራዊ ዕድገት ተመዝግቧል፡፡

ይህ ውጤት የማይታበል የሚታይና የሚጨበጥ እውነት ነው፡፡ በመልካም አስተዳደር ዘርፍ ቀሪ ተግባራት የሉም ባይበልም ፈጥኖ ለማስተካከል የሚቻልባቸው ስልቶች ተቀርጸው እየተተገበሩ ነው፡፡

መንግሥት ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ለመገንባት ሲነሳም መሠረታዊ መነሻው የተጀመረውን ፈጣን ዕድገት ይበልጥ ለማስቀጠል ብሎም የሀገሪቱን ህዳሴ ለማረጋገጥ ነው፡፡ ዋነኛ መተማመኛ ያደረገውም የምልዐተ ሕዝቡን ጉልበት፣ ገንዘብና ዕውቀት ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ይህ ታሪካዊ የሕዝብ ፕሮጀክት በትልቅነቱ በኢትዮጵያ ቀዳሚ መሆኑ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካም ፋና ወጊና ታላቅ ግድብ መሆኑን መገንዘብ ይቻላል፡፡

የግድቡ ግንባታ ሲጠናቀቅ 6 ሺ ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ያመነጫል፡፡ ይህም አሁን ያለውን የሀገሪቱን የኤሌክትሪክ ኃይል በሦስት እጥፍ በማሳደግ ለጎረቤት ሀገሮችም የሚተርፍ ኃይል ለማቅረብ እንደሚያስችል ነው መረጃዎች የሚያመለክቱት በሚፈጠረው 1 ሺ 680 ስኩየር ኪሎ ሜትር ስፋት ያለው ሰው ሠራሽ ሐይቅም የዓሣ ዕርባታ፣ መዝናኛና ሣይንሳዊ ምርምር የሚካሄድበት ቦታ ይሆናል፡፡ እነዚህ የልማት ውጤቶች በዋናነት በኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ተሳትፎና ተጠቃሚነት ላይ የተመሠረቱ መሆናቸው ግልጽ ቢሆንም ሱዳንና ግብፅን ጨምሮ በቀጣናው ለሚገኙ የጎረቤት ሀገራት የሚሰጡት ጥቅም ከፍተኛ መሆኑ የሚታመን ነው፡፡

የኢፌዴሪ የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትር አቶ አለማየሁ ተገኑ በቅርቡ እንደተናገሩት፣ የግድቡ መገንባት ለአገራችን ከፍተኛ ኃይል የማመንጨት አቅም ይፈጥራል። በመነጨው ኃይል ኢንዱስትሪን፣ አገልግሎትንና ግብርናን የማንቀሳቀስ ዕድል፣ የውጭ ምንዛሬ ግኝት፣ ከፍተኛ የዓሣ ምርት፣ የውሃ ላይ ትራንስፖርት፣ የቱሪዝም መስህብ ከመፈጠሩም በላይ የአካባቢውን የአየር ፀባይና ኢኮኖሚም በከፍተኛ ደረጃ ያሻሽላል፡፡ ከአገራት የኢኮኖሚ ዕድገት ጋር ቀጥተኛ ትስስር ያለውን የአገራችንን የነፍስ ወከፍ ውሃ የማከማቸት አቅምም በከፍተኛ ደረጃ ያሳድጋል፡፡

ግድቡ ሱዳንና ግብፅን ከደለልና በክረምት ከሚፈጠር ከባድ ጎርፍ እንደሚታደጋቸው ነው መረጃዎች የሚያመለክቱት። በአካባቢው የሚፈጠረው ፓርክና የዓሣ ምርት ከግድቡ ከ30 ኪሎ ሜትር ባነሰ ርቀት ላይ ለምትገኘው ሱዳን የገበያ አማራጭ እንደሚፈጥርም ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ከምንም በላይ ግን የበካይ ጋዝ ልቀትን ለመቀነስ የተደረገውን ዓለም አቀፍ ስምምነት ለማገዝ ፕሮጀክቱና ተያያዥ ተግባራቱ በምሥራቅ አፍሪካ የራሳቸውን ድርሻ እንደሚጫወቱ ታምኖበታል፡፡

አንዳንድ የኢትዮጵያ ዕድገት የማይዋጥላቸው «የጨለማው ዘመን» ተችዎች «ግድቡ ጥራት የለውም፣ ቢፈርስ ሱዳንና ግብፅን ያጥለቀልቃል» ሳሉ መደመጣቸው አልቀረም፡፡ ይህ ከእውነት የራቀ ተራ ውዥንብር እንደሆነ የሚያስረዱት የፕሮጀክቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጅነር ስመኘው በቀለ ግን ግንባታው በዓለም ላይ የመጨረሻውን የግድብ ግንባታ ቴክኖሎጂና የጥራት ልኬት ተጠቅሞ እየተከናወነ መሆኑን በአፅንኦት ገልጸዋል፡፡

« ዋናው ግድብ 10 ሚሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ያህል ኮንክሪት ሙሌት (RCC) የሚኖረው ሲሆን፤ በስተቀኝ፣ መካከለኛና በስተግራ በሚገኙ ክፍሎች ይከፈላል፡፡ መካከለኛው ክፍል የኃይል ማመንጨት ሥራውን በሚጀመርበት ጊዜ እንደ ማስተንፈሻ ( Spillway) የሚያገለግል ነው፡፡ የኃይል ማመንጫ ቤቶች፣ ማስተንፈሻ፣ የኮርቻ ቅርፅ ያለው ግድብ (Saddle Dam)፣ የኃይል ማከፋፈያ ጣቢያና ሌሎችም ሥራዎች ጥራት ባላቸው ግብአቶች፣ በስታንደርድ ማረጋገጫዎችና ልምድና ዕውቀት ባላቸው ባለሙያዎች የሚከናወኑ ናቸው» ብለው፤ የግድቡን ጤንነት መጠበቅ ለሌላ ሀገር ተብሎ ሳይሆን ለብሔራዊ ጥቅምና ለጋራ ዕድገት ካለው ወሳኝ ድርሻ አንፃር የሚታይ መሆኑንም አስምረውበታል፡፡

የታላቁ የህዳሴ ግድብ የመሠረት ድንጋይ ሲቀመጥ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ ያደረጉት ንግግር የግድቡን አህጉራዊ ፋይዳ በግልፅ ያሳያል፡፡«... ታላቁ የህዳሴ ግድብ ድህነትን ለማጥፋት ያለንን ቁርጠኝነት ማሳያና የተፋሰሱ ሀገራትን የጋራ ጥቅም የሚያስከብር ትብብር ለመፍጠር ያለንን ዝግጁነት በተግባር የሚያረጋግጥ ምስክር ነው፡፡ የዚህ ታላቅ ግድብ ጥቅም በኢትዮጵያ ብቻ የተወሰነም አይደለም፡፡ ይልቁንም ሁሉንም ጎረቤቶቻችንን በተለይም የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት የሆኑትን ሱዳንንና ግብፅን በእጅጉ የሚጠቅም ትልቅ ፕሮጀክት ነው፡፡» ነበር ያሉት ፡፡

ታላቁ የህዳሴ ግድብ ከሀገር አልፎ አህጉራዊ ትልቅነት ያለው ከላይ በተጠቀሱት ነጥቦች ብቻ አይደለም፡፡ ይልቁንም ከሦስት መቶ ሃምሳ ሚሊዮን በላይ ሕዝብ የሰፈረባቸው የናይል ተፋሰስ ሀገራት የጋራ ሀብትን በወል የመጠቀም አስተሳሰብንና መተማመንንም ስለሚፈጥር ነው፡፡ ማንኛውም ሀገር ቢሆን በሰጥቶ መቀበልና የጋራ ተጠቃሚነት መርህ ( win win approach ) እንዲመራ የሚያስችል ቋሚ ሐውልት በመሆኑም ነው፡፡ የፕሮጀክቱ ሂደት ከኖረና የተዛባ የውሃ አጠቃቀም አስተሳሰብ አውጥቶ ፍትሐዊና መተማመን የሰፈነበት ግንኙነት ለመፍጠር የሚያስችል ስለሆነም ነው ፡፡ ይህ እውነታ ደግሞ በአፍሪካም ታላቅ የዘመናችን ፕሮጀክት እንዲሆን ያደርገዋል፡፡
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment