Wednesday, November 27, 2013

«በአገራችን ሠርተን መለወጥ፤ አገራችንንም ማገልገል እንፈልጋለን» - የሳዑዲ አረቢያ ተመላሾች

(Nov 26, 2013, (አዲስ አበባ))--በሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ ውስጥ በርካታ የሳዑዲ አረቢያ ተመላሾች ተሰብስበው ያወጋሉ፤ ይጫወታሉ። ሕፃናት ልጆቻቸውም ሜዳ ላይ ከወዲያ ወዲህ ይሯሯጣሉ። ከፊሉ ደግሞ ወደ ትውልድ ቀያቸው የሚሸኛቸው አውቶብስ ተሰልፈው በመጠባበቅ ላይ ናቸው። የተለያዩ መለዮዎችን የለበሱ የበጎ ፍቃድ አገልጋዮችም የተመላሾቹን ሻንጣዎች ተሸክመው ወደ የአውቶቡሱ በማስገባት ይደግፏቸዋል። ከቤተሰቦቻቸው መገናኘት ያልቻሉትንም በግል ስልካቸው ሳይቀር በመደውል ለማገናኘት የበኩላቸውን ጥረት ያደርጋሉ።

ሳዑዲ አረቢያ የሚገኙት ወንድሞቿ በሀገሯ ሆና እንድትሠራ የመከሯትን ምክር ባለመቀበል በሕገወጥ መንገድ ከሀገር መውጣቷን የምትናገረው ሠናይት አምሮ እዚያ እንደደረሰች ያጋጠማት ነገር ፈፅሞ ያልጠበቀችው መሆኑን ትጠቅሳለች። «አረብ ሀገር ብር የሚታፈስ ይመስለኝ ስለነበር የወንድሞቼን ምክር አሻፈረኝ ብዬና የነበረችኝን ካፍቴሪያ ዘግቼ ስሄድ የጠበቀኝ መገፋትና እንግልት ብቻ ነበር። በሁለት ዓመት ቆይታዬ ምንም ጥሪት አላፈራሁም። በድንገት ሀገር ለቀን እንድንወጣ በመደረጉም የአምስት ወር ደመወዜን ሳልቀበል ነው ባዶ እጄን የመጣሁት» ትላለች።

ከአገር የወጣችው በሕገወጥ መንገድ ስለነበርም የኢትዮጵያ መንግሥት «ይቀበለኛል» የሚል ግምት እንዳልነበራት የምትናገረው ሠናይት፣ ሀገር ውስጥ ከገባች በኋላ መንግሥትና ሕዝብ እንደ ምግብና መጠለያ ያሉት ድጋፎች ስለተደረገላት ከፍተኛ የሆነ ደስታ እንደፈጠረባት ታስረዳለች።

«የስደትን ጦስ አይቼዋለሁ። አገር እያለኝ አገር እንደሌለው ስንከራተት ቆይቻለሁ። ከዚህ በኋላ በአገሬ ሰርቼ መለወጥ ብቻ ነው የምፈልገው» በማለት ትናገራለች። ወደ ትውልድ ስፍሯዋ እንደደረሰችም እንደቀድሞው ምግብ ቤት ከፍታ በመሥራት አገሯንና ሕዝቧን ለማገልገል ቆርጣ መነሳቷን ነው ያመለከተችው። እንደ እርሷ ያሉ ወጣቶች ከእርሷ ሕይወት ተምረው በአገራችው ውስጥ ሆነው ተባብረው ራሳቸውንና አገራቸውን መለወጥ ያለባቸው መሆኑንም ምክር ሰጥታለች።

ሕፃን ልጇን ጡት እያጠባች ያገኘናት ወይዘሮ ዛሃራ አብዱልናስር ለአምስት ዓመታት ከነቤተሰቧ በስደት በሳዑዲ አረቢያ የኖረችበትን ጊዜ ማስታወስ እንደማትፈልግ ትናገራለች። በተፈጠረው ችግር ባዶ እጇን መምጣቷና ከባለቤቷ በመለያየቷ ከፍተኛ የሆነ የሥነ ልቦና ጫና እንዳጋጠማት ትገልፃለች ።

«ይሁንና ከትናንት በስቲያ አገሬ ከገባው በኋላ መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ ስላደረገልኝ ከነበረብኝ ፍርሃትና ኀዘን እየወጣሁ ነው» የምትለው ወይዘሮ ዛሃራ፤ በዩኒቨርሲቲው ካረፈችበት ቀን ጀምሮ በቆይታዋ በመንግሥትና በበጎ ፍቃደኛ አገልጋዮች የተደረገላት ድጋፍ ወገን እንዳላትና ብቻዋን እንዳልሆነች እንዳመለከታት ትገልፃለች።

«አሁን የምፈልገው አገሬ ውስጥ ያገኘሁትን ሥራ ሠርቼ ማደግ ብቻ ነው» የምትለው ከስደት ተመላሽዋ ወይዘሮ ዛሃራ፤ ከመንግሥት ብድር ማግኘት ከቻለች በንግድ ሥራ ተሰማርታ ኑሮዋን የማሻሻል ሃሳብ እንዳላት ነው የጠቆመችው፡፡

በበጎ ፍቃደኝነት ከስደት ተመላሾቹን ሲደግፉና ሲረዱ ያገኘናቸው ወጣት አብርሃ አፅብሃና አንዋር ሁሴን ደግሞ እንደ ዜጋ የሚጠበቅባቸውን ግዴታ መወጣት በመቻላቸው ከፍተኛ ደስታ እንደተሰ ማቸው ነው ያስረዱት። ከየካ ክፍለ ከተማ ወጣቶች ሊግን ወክሎ የመጣው ወጣት አብርሃ እንደሚለው ስደተኞቹን መቀበል ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ቀንና ሌሊት ከቦሌ ኤርፖርት እስከ ማረፊያቸው ድረስ የሚያስፈልጋቸውን ድጋፍ ያለመታከት እየሰጡ ነው። «ከስደት ተመላሾቹ ሕፃናት ልጆቻቸውንና ሻንጣቸውን ይዘው እንዳይንገላቱ እንረዳቸዋለን። ሻንጣቸውን ተሸክመን ወደሚፈ ልጉበት አቅጣጫ እንሸኛቸዋለን» በማለትም ይናገራል።

የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር አዲስ አበባ ቅርንጫፍ የበጎ ፍቃድ አገልጋይ የሆነው ወጣት አንዋር ሁሴን በበኩሉ «የአካል ጉዳትና የሥነልቦና ችግር ያጋጠማቸውን ተመላሾች ወደ የጤና ጣቢያው የአምቡላንስ አገልግሎት የመስጠት ሥራ እየሠራ ነው» ይላል። እርሱ እንደሚለው፤ ተጎጂዎቹን ወደ ጤና ጣቢያ ከማድረስ በዘለለ ማህበሩ ከቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲገናኙ የስልክ አገልግሎት በነፃ እየሰጣቸው ይገኛል።

በአደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች አስተባባሪ አቶ አስመላሽ ገብረ ሕይወት በበኩላቸው እንደገለጹት፤ በየቀኑ ከ400በላይ ሰዎች በመቀበል አስፈላጊው ድጋፍ እየተደረገላቸው ነው። በአሁኑ ወቅትም የተለያዩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት በጋራ በመሆን ለስደት ተመላሾቹ ከአየር መንገድ ጀምሮ በመቀበል የምግብ የመኝታና የትራንስፖርት አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን ይጠቁማሉ።

«በቆይታቸው ወቅት ምግብ፣ መኝታ እንዲሁም የህክምና አገልግሎት በነፃ ያገኛሉ። ወደየትውልድ ስፍራቸው መመለሻም የሚሆን 900 ብር ይሰጣቸዋል» የሚሉት አስተባባሪው፤ ከዚህ በተጨማሪም አንዳንድ በጎ ፍቃደኞች ያለውን ችግር መጥተው ካዩ በኋላ ለሕፃናቱ የሚሆን 48 ቆርቆሮ ወተትና የተለያዩ አልሚ ምግቦችን እንዲሁም 425 የሴቶች የንፅህና መጠበቂያ ድጋፍ ያደረጉላቸው መሆኑን ነው የሚያመለክቱት። ባለሀብቶችም አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ቃል የገቡበት ሁኔታ መኖሩንም ያስታውሳሉ።

እስካሁን ከ33ሺ በላይ ዜጎች ወደ አገር ቤት መመለሳቸውን የሚያመለክቱት አቶ አስመላሽ፤ በቀጣዩቹ ቀናት ይመጣሉ ተብሎ የሚጠበቁትን 45ሺ የሚሆኑ ዜጎች አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ከባለድርሻ አካላትና ከባለሀብቶች ጋር በመተባበር እየተሠራ መሆኑን ነው የገለጹት። በቅርቡም እስከ ሦስት ሺ ሰዎች ማስተናገድ የሚችል ማረፊያ ተዘጋጅቶ አገልግሎት የሚሰጥ መሆኑን ነው ያስታወቁት።
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment