Wednesday, October 30, 2013

ወደ አረብ አገሮች የሚደረጉ ጉዞዎችን የሚመለከቱ አሰራሮችና ህጎች ይከለሳሉ

(Oct 30, 2013, (አዲስ አበባ))--ዜጎች ወደ አረብ አገሮች የሚያደርጓቸው ጉዞዎችን የሚመለከቱ ህጎችና አሰራሮች ተፈትሸው የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶች ለማስከበር በሚያስችል መልኩ እንደሚዘጋጁ ተገለጸ። የኢፌዴሪ የሰራተኛና የማህበራዊ ጉዳይ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሮችና የፌዴራል ፖሊስ የሥራ ኃላፊዎች በጋራ በመሆን ወደ አረብ አገራት የሚደረገው ጉዞ በጊዜያዊነት መታገዱን ምክንያት በማድረግ ትናንት ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።

የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ዘሪሁን ከበደ እንደገለጹት፤ ጊዜያዊ እገዳው የተጣለው ወደ አረብ አገሮች ለሥራ በሚሄዱ ዜጎች ላይ የሚደርሰውን እንግልትና ስቃይ ለመከለከል ነው። «እገዳው እስከ ሰባት ወር ድረስ ይቆያል። ህጎችና አሰራሮቹ ከተከለሱ በኋላ ይነሳል ተብሎ ይጠበቃል» ብለዋል።

«በአሁኑ ወቅት ያሉ የውጭ የሥራ ሥምሪት ህጎች የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶችን የሚያስከብሩ አይደሉም» ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ አንድ ሰው በቀን ለስምንት ሰዓታት መስራት ያለበት ቢሆንም በአረብ አገራት በተለይ በቤት ሰራተኝነት የሚሰማሩ ዜጎች በቀን እስከ 12 ሰዓታት እንደሚሰሩ ተናግረዋል።

ወደ አረብ አገራት ዜጎች ሲልኩ የነበሩ የሥራና ሰራተኛ አገናኝ ድርጅቶች ህጋዊና ህገ ወጥ ድርጊቶች እየቀላቀሉ ይሰሩ እንደነበር የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ድርጅቶቹ ከህገ ወጥ ደላሎች ጋር በትብብር ይሰሩ እንደነበር አመልክተዋል። እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ገለጻ፤ ድርጅቶቹ ሰራተኞች ወደ ውጭ ከላኩ በኋላ ደህንነታቸውን ያለመከታተል ችግር ይታይባቸዋል። አብዛኛዎቹ ድርጅቶች ሰራተኞቹን ለመከታተል የሚያስችል አቅም እና አደረጃጀት የላቸውም።

ዜጎች ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሰው የመስራት መብት እንዳላቸው አስታውሰው፤ ይሁንና ይህ መብት ደህንነታቸውን አደጋ ወስጥ በማይከት መልኩ መፈጸም እንዳለበትም ጠቁመዋል። ሚኒስትር ዴኤታው እንደተናገሩት፤ በ 2003 በጀት ዓመት ወደ አረብ አገራት የተጓዙ ዜጎች ቁጥር 14ሺ ነበር፤ በ 2004 ወደ 42 ሺ ከፍ ያለ ሲሆን፤ በ 2005 ደግሞ ከ 198 ሺ በላይ ደርሷል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዜጎች ጉዳይ ክትትልና ድጋፍ ዳይሬክተር አቶ ጣፋ ቱሉ እንደገለጹት፤ ለሥራ ወደ አረብ አገራት የሚጓዙ ዜጎች ከአቅም በላይ ሥራ፣ ድብደባና እንግልት እንዲሁም የለፉበትን ክፍያ ያለማግኘት ችግሮች እያጋጠሟቸው ነው። በመሆኑም ችግሮቹን ለማስወገድ የማሻሻያ እርምጃዎችን መውሰድ ተገቢ ነው።

በፌዴራል ፖሊስ የተደራጁ ወንጀሎች ምርመራ አስተባባሪ ዋና ኢንስፔክተር ወንድሙ ጫማ እንደገለጹት፤ እገዳን ምክንያት በማድረግ በህገ ወጥ መንገድ ዜጎችን ለማስኮብለል የሚደረገውን ህገ ወጥ እንቅስቃሴ ለመከላከል ፖሊስ ኃላፊነቱን በብቃት ለመወጣት ተዘጋጅቷል። የሥራ ኃላፊዎቹ ህብረተሰቡ የጊዜያዊ እገዳውን አስፈላጊነት በመገንዘብ ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውር ለመከላከል ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪያቸውን አቅርበዋል። እገዳው በሚነሳበት ወቅት መንግሥት በመገናኛ ብዙኃን ያስታ ውቃል።

እገዳው በተለይ በቤት ሰራተኝነት ለመሰማራት ወደ አገሮቹ በሚያመሩ ዜጎች የሚመለከት እንጂ ለኢንቨስትመንት፣ ንግድና ሌሎች ጉዳዮች ለሚጓዙ ዜጎች እንደማያካትትም ተመልክቷል።
ከአዲስ ዘመን

No comments:

Post a Comment