Sunday, March 01, 2020

ይድረስ ለአዲሱ ፈርኦን, ምድረ ግብፅ (በተመስገን አፈወርቅ)

ዝ ጦማር ተፅህፈ... እምነገደ ኢትኦጲስ አሳቢ
ከምደረ ሀበሻ ተረተር.... ከአባይ ፈትፍቶ ቀላቢ
ሰላም ለከ ንዑስ ፈርዖን...ግብፀ ልዑል አቃቢ

ገድለ ኦሪት የዘከረው...ያባትህ እብሪት ቱማታ
የአብርሃምን ዘር በባርነት...ለምዕተ ዓመት ሲገታ

የፒራሚዶቹ ሾሌ... በአምላክ ክብር እንዳነጣጠሩ
ልጆቹን አርነት እንዲለቅ... ጌታ ቢያዘው ከመንበሩ
እምቢታው ነበር ውጦ... ያስቀረው አዘቅት ሆኖት ከባህሩ

አቡከ ናቡከደነፆር...የአምላክ ትእዛዝ ናሙና
የሙሴን ህብስተ መና ...የጽፅዮንን ሙዳየ ጥና
የዳዊትን እንዚራ ቃና... የዮርዳኖስን በገና
ቤተ እስራኤል እንዳያጣጥም... ከተስፋው ጎጆ እንዳይፀና

በባርነት ሰቅዞ ይዞ በካይሮ ሰንሰለት ጥማዱ
እምቢታው ነበር የፈጀው የዳጠው በአምላክ ክንዱ

የእርግማን ንግርት ይመስል... ዛሬም የውሃ ጦስ ምልኪያን
ይህው ሽህ ዘመንን ቆጥሮ... ቀሰፈው ምስራቅ አፍሪካን

አድምጠኝ አዲሱ ፈርዖን... ውሉደ እብሪት ቱማና

በሰው ደም ፒራሚድ ማነፅ... በሰው ደም መስኖ አሽታ
ይብቃ ዘንድሮ ይብቃ...በሰው መክሊት ሸመታ

ኢትዮጵያ በርሃብ ስትረግፍ... በጎርፍዋ ሰብል ይታጨድ?
ካይሮ ገላ ሲታጠብ... ሀበሻ በጥም ይስደድ?
አይበቃም ያባትህ መዘዝ ካደራ ልጆች መጓደድ?

የእመብርሃን አስራት ቤት... ከአንድዬ ማረፊያ በራፍ
ከግማደ መስቀሉ ማረፊያ... ከፅዮን ፅላት መኩዋረፍ

ይብቃ ባባትህ ይብቃ... ዳግም በባህር አትስመጥ
ታሪክ እንደከተበው... ውሃነው ማብቂያው የቀበጥ

ተለመን አዲሱ ፈርዖን... ውሉደ ናቡከደነዖር
አበሻ ይሉኝን እንጂ...አይፈራም ዘገርና ፆር

ሀበሻ የእንቅልፍ ያህል... ሲነቃ ከእባብ ይከፋል
ካብህን አይነካም እንጂ... ለካቡ ሞትም ይልሳል

በፀባይ ሲገድሉት እንጂ...በእብሪት ጉንጩን አይሳም
ትዕግስቱ ይዳፈን እንጂ ...ሲነኩት ሞቶም አይረሳም

ተመስገን አፈወርቅ (አዲስ ዘመን ጋዜጣ)
ነሐሴ 2002 ዓ.ም         

No comments:

Post a Comment