Tuesday, May 28, 2013

የአባይ ወንዝ ፍሰትን የማስቀየስ ስራ ተከናወነ

(May 28, 2013, (አዲስ አበባ))--የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የግድቡ ኮንክሪትና መሰረት የሚያርፍበት ወሳኙን ስራ ለማከናወን የአባይ ወንዝ ተፈጥራዊ ፍሰቱን  የማስቀየስ ስራ  ግንቦት 20 /2005 ተከናውኗል፡፡

በዚሁ ስነ ስርአት ላይ የተገኙት የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ህዝባዊ ተሳትፎ አሰተባባሪ ምክር ቤት  ፕሬዝዳንት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን እንዳሉት የግንቦት 20 ፍሬ የሆነውን ታላቁ ግድባችን  ለህዝባችን ጥቅም ለማዋል የወንዙ ፍሰት አቅጣጫ በምንፈልገው መንገድ የማስቀየስ ስራ ተከናውኗል፡፡

 የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለሀገራችን ጥቅም ብቻ ሳይሆን ለጎረቤታችንም ጭምር ነው ፡፡የግድቡ ግንባታ ከተጀመረ ወዲህ ግንባታውን ለማሳካት የተለያዩ ስራዎች እንደተከናወኑ ሁሉ ፍሬውን ለማየት ለግድቡ ስኬትና ፍፃሜ የኢትዮጵያ ህዝብ የጀመረውን አስተዋፅኦ አጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል፡፡

የታላቁ መሪ መለስ ዜናዊና የሰማእታት አደራን ተቀብለን አላማቸውን ህያው በማድረግ የኢትዮጵያን ህዳሴ ለማብሰር በትኩረት ይሰራል ብለዋል፡፡

 በታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ አመንጭነት በ2003 ዓ/ም መጋቢት 24 ግንባታው የተጀመረው  የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ  አጠቃላይ ግንባታው 21 በመቶ ተጠናቋል፡፡ 6 ሺህ ሜጋ ዋት የማመንጨት አቅም ያለው የታላቁ የህዳሴ ግድብ ከ 5 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ፈጥሯል፡፡

 1200 ማሽነሪዎች በግድቡ ግንባታ ስራ ተሰማርቷል፡፡ ለግንባታው አጋ¡ የሆነው 247 ሜትር ርዝመት ያለው ድልድይ የተገነባ ሲሆን በሰአት 800ሜትር ኩብ የኮንኩሪት ድንጋይ የሚፈጭ ፋብሪካም ተገንብቷል፡፡የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታው ሲጠናቀቅ 74 ቢሊዮን ሜትር ኩብ ውሃ የመያዝ አቅም አለው፡፡ 
ምንጭ፡ ኢሬቴድ

No comments:

Post a Comment