Wednesday, May 15, 2013

ኮሚሽኑ የፀረ ሙስና ትግሉን በሌሎች ተቋማት ላይም ይቀጥላል

(May 15, 2013, አዲስ አበባ))--የፌዴራል የሥነ ምግባርና የጸረ ሙስና ኮሚሽን የጸረ ሙስና ትግሉን በሌሎች ተቋማት ላይ በጥናት ተመስርቶ እርምጃ ለመውሰድ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን አስታወቀ። የኢፌዴሪ አራተኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ትናንት ባካሄደው የሦስተኛ ዓመት የሥራ ዘመን 27ኛ መደበኛ ስብሰባው የፌዴራል የሥነ ምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የ2005 በጀት ዓመት የአሥር ወራት የእቅድ አፈጻጸም ሪፖርትን አዳምጧል።

የኮሚሽኑን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ያቀረቡት ኮሚሽነሩ አቶ አሊ ሱለይማን እንደገለጹት፤ ሰሞኑን በኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከፍተኛ ኃላፊዎችና ሌሎች ግለሰቦች በሙስና ተጠርጣሪዎች ላይ የተወሰደው እርምጃ በሌሎች ተቋማት ላይም ለመቀጠል የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡ ይህም «ጥናቱ ተጠናቅቆ ሕጋዊ ሥርዓቱን በተከተለ መልኩ እርምጃ ለመውሰድ የሚያስችል ሁኔታ ሲፈጠር ተግባራዊ ይደረጋል» ብለዋል፡፡

እንደ ኮሚሽነሩ ገለጻ፤ ከእነዚህ የትኩረት አቅጣጫዎች መካከል አንዱ በኢትዮጵያ ገቢዎች እና ጉምሩክ ባለሥልጣን አካባቢ ያለው የገቢ አሰባሰብ ሁኔታ ነው፡፡ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በህይወት እያሉ ከሁለት ዓመት በፊት ጥናቱ ተጀምሮ በዚያው ወቅትም ወደ መጠናቀቁ ደርሶ ነበር። ሆኖም የጠቅላይ ሚኒስትሩ በድንገት ከዚህ ዓለም በሞት መለየት ጋር በተያያዘ በተፈጠረው ሀዘን ተጠርጣሪዎቹን በቁጥጥር ስር የማዋልና በሕግ ተጠያቂ የማድረግ እርምጃ ለመውሰድ ትንሽ ቢዘገይም ሂደቱ በዘመቻ ሳይሆን በበቂ ጥናት ላይ ተመስርቶ የተከናወነ ነው፡፡

«እስከ አሁን ድረስ የህዝብ እሮሮዎችን እየተከተልን በጥቃቅን ጉዳዮች ላይ ሳይቀር ስንሰራ ቆይተናል» ያሉት ኮሚሽነሩ፤ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ ተግባራዊ መደረግ ከጀመረ ጊዜ አንስቶ ኮሚሽኑ ዋና ዋና የትኩረት መስኮችን ለይቶ በመንቀሳቀስ ላይ እንደቆየ ተናግረዋል፡፡ በእነዚህ የትኩረት መስኮች ውስጥ ከተካተቱት ተቋማት አንዱ የመንግሥት ገቢ አሰባሰብ ላይ ያለውን ችግር መለየት መሆኑን ጠቅሰው፤ ሰሞኑን የተወሰደውም እርምጃ የእዚሁ አካል መሆኑን ነው ያብራሩት። በመሥሪያ ቤቱ ላይ ክትትሉ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡

ኮሚሽነሩ እንደገለጹት፤ በቀጣይም ከፍተኛ የመንግሥት ሀብትና ንብረት ሥራ ላይ የሚውልባቸው፣ ከፍተኛ በጀት ተጠቃሚ የሆኑ እና ተደጋጋሚ የሕዝብ ቅሬታ የሚስተዋልባቸው ተቋማት ላይ አሁንም የማጣራት ሥራ ይከናወናል፡፡

የምክር ቤቱ አባላት በበኩላቸው «እርምጃው ለምን አንድ መስሪያ ቤት ላይ ብቻ ሆነ? በቀጣይስ ሌሎች መሥሪያ ቤቶች ይሄን እርምጃ ተመልክተው መረጃ አይሰውሩም ወይ?» የሚሉ ጥያቄዎችን አንስተዋል። ኮሚሽነሩ በሰጡት ምላሽም ፤ «እየተካሄደ ያለው ተግባር የዘመቻ ሥራ ሳይሆን በበቂ ጥናት ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ እርምጃ ለመውሰድ በቂ የሰው እና የሰነድ ማስረጃ ይፈልጋል» ብለዋል፡፡ «ሊጠፉ ይችላሉ » ለሚለውም ስጋት ኮሚሽኑ ከህዝቡ ጋር በጋራ ስለሚሰራ ከህዝብ የሚያመልጥ እንደማይኖርም ነው የገለጹት፡፡

«ሙስናን መዋጋት ሕግን ተከትሎ የሚከናወን ተግባር ነው» ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ሙስናን ለመከላከል ሲባል ሌሎች በሕገ-መንግሥቱ የተደነገጉ የዜጎች መብቶችን መስዋዕት በማድረግ እንዳልሆነ አብራርተዋል። «እርምጃ ስንወስድ በቂ መረጃዎች እንዲሁም መረጃዎቹን የሚያጠናክሩ በቂ ማስረጃዎች አሉን ወይ? የሚለውን መመለስ ነበረብን» ሲሉም አስረድተዋል፡፡

«ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ አንድም የተያዘ ሰው የለም፤ ወደ ተጠርጣሪዎች ላይ እርምጃ ሲገባም በሕገ መንግሥቱና በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓቱ ሕግ ላይ የተቀመጡ ሥርዓቶችን በተከተለ መልክ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ አውጥተናል፤ የመኖሪያ ቤት ሲፈተሽም የመፈተሻ ሥርዓትን ተከትለን ያከናወነው ተግባር ነው፤ በመሆኑም በአፈጻጸም ውስጥ ያጋጠመ አንድም የሕግ ክፍተት የለም» ብለዋል፡፡

«ተጠርጣሪዎች ላይ የተወሰደው እርምጃ ቆራጥነት የተሞላበት ቢሆንም ከጊዜ አኳያ ሕዝቡ አምርሮ በመንግሥት ላይ ጥርጣሬ ካሳደረ በኋላ የተወሰደ ነው» በሚል ከምክር ቤቱ አባላት የቀረበውን አስተያየት በተመለከተ ኮሚሽነሩ በሰጡት ምላሽ፤ «ሙስና የሥርዓቱ አደጋ ነው፡፡ ከዛ የከፋው ደግሞ የሰብአዊ መብት ገፈፋ እጅግ የከበደ ይሆናል፡፡ በመሆኑም አንዱን ስናስከብር ሌላውን መጣስ ስለማይገባ የሁለቱን ሚዛን አስጠብቆ ለማስኬድ ወደ እርምጃው ለመግባት ጊዜ ወስዷል፡፡ ለዚህ ደግሞ "ኮሽ ባለ ቁጥር ተኩስ አይከፈትም» ብለዋል፡፡

የኮሚሽኑን የአስር ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ያዳመጡት የምክር ቤቱ አባላትም ሰሞኑን በተጠርጣሪዎች ላይ የተወሰደው እርምጃ ዓይነት ተግባር ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው ነው ያስታወቁት፡፡

የሕግና ፍትሕ አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ሚሊዮን አሰፋ በበኩላቸው፤ የኮሚሽኑ የለውጥ ግንባታ የሚገኝበትን አፈጻጸም ማሻሻል፤ አገልግሎት አሰጣጡን ማቀላጠፍ፤ ለተቋሙ ድጋፍ ሊያደርጉ የሚችሉት የተቋሙ ረቂቅ ሕጎች በአጭር ጊዜ እንዲጸድቁ ማድረግ፤ ከባለድርሻ አካላት ጋር የተቀናጀ ተሳትፎ ለማረጋገጥ ማስቻል፤ በውስጡ ያሉ ችግሮችን ማስወገድ፤ የኦዲት ሥራዎችን ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡

በፀረ ሙስና ትግሉ የሕዝብ ተሳትፎን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ልዩ ልዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን ማከናወኑ፤ ከዜጎች የሚደርሱ ጥቆማዎችንና አቤቱታዎችን በመቀበል ተገቢው ውሳኔ መሰጠቱ፤ ሙስናና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል በታላላቅ የመንግሥት ፕሮጀክቶች መደበኛ በሆነ መልኩ የአሰራር ጥናቶች ማካሄድ መጀመሩን በጠንካራ ጎን ተነስተዋል፡፡ 
ምንጭ፡አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment