Thursday, February 28, 2013

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን 6ኛውን ፓትሪያሪክ መረጠች

(Mar 01, 2013,አዲስ አበባ)--ብፁዕ አቡነ ማትያስ ከምርጫው በኋላ «እግዚአብሔር የፈቀደውን አድርጓል እኔም ጥሪውን በአክብሮት ተቀብያለሁ» ብለዋል፤ ለስድስተኛው ፓትርያርክ ምርጫ በዕጩነት ከቀረቡት አምስት ብፁዓን ሊቀ ጳጳሳት በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማትያስ 500 ድምፅ በማግኘታቸው ስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ሆነው ተመረጡ።


በዓለ ሲመታቸውም የካቲት
24 ቀን 2005 .ም ከሌሊቱ አስር ሰዓት ጀምሮ በመንበረ ፀባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል መላው ካህናትና ምዕመናን በተገኙበት ይካሄዳል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስትያን ፓትርያርክ ምርጫ ትናንት የምርጫ ታዛቢዎች በተገኙበት በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ አቡነ ናትናኤል አቃቤ መንበረ ፓትርያርክ እና የአርሲ አገረ ስብከት በፀሎት አስጀምረው የመጀመሪያም መራጭ ሆነዋል።መራጮችም ቃለ መሃላ ከፈፀሙ በኋላ በየተራቸው ድምፅ ሰጥተዋል።

በምርጫውም ከግብፅ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ኦፕቲክ ቤተ ክርስቲያን የመጡ አምስት ሊቃነ ጳጳሳት ድምፅ ሰጥተዋል። ለመራጭነት ከተመዘገቡት 808 መራጮች መካከል 806 ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ፣ካህናትና ምዕመናን ድምፅ መስጠታቸውንና የምርጫ ሥነ ሥርዓቱም ከቀኑ630 መጠናቀቁን የጅማ አገረ ስበከት ሊቀ ጳጳስና የአስመራጭ ኮሚቴው ሰብሳቢ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ አመልክተው፤ ታዛቢዎች በተገኙበት በተደረገው የድምፅ ቆጠራ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማትያስ 500 ድምፅ በማግኘት በፓትርያርክነት መመረጣቸውን ገልጸዋል።

ምርጫውም ትክክለኛና ያለምንም እንከን የተካሄደ ለመሆኑ የምርጫ ታዛቢዎች ለአስመራጭ ኮሚቴው ማረጋገጣቸውንም ገልጸዋል። ምርጫው በተያዘለት መርሀ ግብር መሠረት እንዲጠናቀቅ በፆምና በፀሎት ሲያግዙ የቆዩትን በአስመራጭ ኮሚቴው ስም ምስጋና አቅርበው ላደረጉት ሁሉ እግዚአብሔር ዋጋቸውን እንዲከፍል ፀሎታቸው እንደሆነ ተናግረዋል።

ከምርጫው በኋላ ተመራጩ ብፁዕ አቡነ ማትያስ «እግዚአብሔር የፈቀደውን አድርጓል፤ እኔም ጥሪው በአክብሮት ተቀብያለው በማለት ገልጸዋል» ምንም እንኳን የቤተክርስቲያን ሥራ ከባድ ቢሆንም ከአበው ሊቃነጳጳሳት ከካህናትና ከምዕመናት ጋር ሥራው የቀለለ ይሆናል ብዬ አምናለሁ ብለዋል።

የምርጫው ታዛቢ ከሆኑት ውስጥ ከፌዴራል ጉዳዮች ወይዘሮ ፈንታዬ ገዛኸኝ እና ከአገር ሽማግሌዎች ደግሞ ኢንጂነር ጌታቸው ማህተመሥላሴ እንደተናገሩት፤ ምርጫው ሥነሥርዓት ያለውና የተረጋጋ ነው።በሰዓቱ ተገኝተው ሁሉም ቅድመ ሁኔታ መሟላቱንና የምስጢር ድምፅ መስጫ ሳጥኑም በግልፅ የሚታይ መሆኑን አስተውለዋል።

የመተከል አገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መላከሰላም ብርሃነዓለም እና የደብረ ይባቤ ቅዱስ ያሬድ ቤተ ክርስቲያን የሰበካ ጉባኤ አባል ወይዘሮ ሶስና መኮንን ድምፅ ከሰጡ በኋላ እንደገለጹት፤ ምርጫው መንፈሳዊና ፍትሃዊም ጭምር ነው።እግዚአብሔር አምላክ ደግሞ የወደደውን ያስቀምጥ ዘንድ በፀሎት ሲማፀኑት ቆይተዋል። መልካሙንም እንደሚያደርግ ነው።

በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ኃላፊና የአስመራጭ ኮሚቴው አባል መላከ ሰላም አምደብርሃን ገብረፃድቅ እንደተናገሩት፤ ከብፁዕ ወቅዱስ ተክለሃይማኖት ሦስተኛ ጀምሮ የተደረጉትን ምርጫ ተከታትለዋል። በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስም መራጭ እንደነበሩ አስታውሰው፤ አሁን ከተካሄደው ምርጫ ጋር ሲያነፃፅሩት የመራጩ ቁጥር ከመጨመሩም በላይ ሂደቱ እየተሻሻለ ሰጥቷል።

መልካም የምርጫ ሂደቶች መስተዋላቸው ጠቅሰው፤ በአብ ነትም ከግብፅ እህት ቤተ ክርስቲያን ከሆነችው ከግብፅ ጋር የተፈጠረው መቀራረብ እንዳስደሰታቸው ገልፀዋል። ስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ሆነው የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ማትያስ አስራት በቀድሞው ትግራይ ክፍለ አገር በአጋሜ አውራጃ በስቡሕ ወረዳ በ1934 .ም ከአባታቸው ከአቶ ወልደጊዮርጊስ እና ከእናታቸው ከወይዘሮ ከለላ መወለዳቸውን ከሕይወት ታሪካቸው ማወቅ ተችሏል።

አቡነ ማትያስ ከሃይማኖታዊ እውቀታቸው በተጨማሪ ከፍተኛ የሆነ ዓለም አቀፋዊ ተሞክሮ ያላቸው አባት ሲሆኑ፤ ከአገር ውስጥ ቋንቋዎች በተጨማሪ እንግሊዝኛ፣ ዕብራይስጥ፣ ግሪክ እና ዐረብ ቋንቋዎችን በሚገባ መቻላቸው ተጠቁሟል።
አዲስ ዘመን ጋዜጣ 

No comments:

Post a Comment