Monday, November 26, 2012

የአዲስ አበባ 125ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል ተጠናቀቀ

(Nov 26, 2012, Reporter)--ላለፈው አንድ ዓመት በተለያዩ ዝግጅቶች በተለያዩ ቦታዎች ሲከበር የቆየው የአዲስ አበባ ከተማ 125ኛ ዓመት የምሥረታ ክብረ በዓል፣ ቅዳሜ ኅዳር 15 ቀን 2005 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ስታዲየም ተከብሮ ተጠናቋል፡፡

በመዝጊያው ፕሮግራም ላይ የአገሪቷ ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ አምባሳደሮች፣ የተለያዩ አገሮች እህት ከተሞች ከንቲባዎችና ተወካዮች፣ የክልል ከተሞች ከንቲባዎች፣ እንዲሁም የመከላከያ ሠራዊት አመራሮች በተገኙበት ተከናውኗል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ ኩማ ደመቅሳ በዕለቱ ባደረጉት ንግግር፣ የኢትዮጵያና የአፍሪካ ኅብረት ማዕከል የሆነችው አዲስ አበባ ዕድገቷ በዕድሜዋ አንጋፋነት ልክ የተፋጠነ እንዳልሆነ፣ ከተማዋ በሁሉም መስክ አንድ ከተማ ሊያሟላ የሚገባውን ልማት ሳታሟላ ከአንድ ምዕተ ዓመት በላይ እንዳስቆጠረች፣ በነገሥታቱ ዘመን የከተማዋ የመሬት ይዞታ ለመኳንንት፣ ለመሳፍንትና ለጦር አበጋዞች ተከፋፍሎ አብዛኛው የከተማዋ ነዋሪዎች ሲሰቃዩ እንደኖሩ፣ የከተማዋ ዕድገት ማስተር ፕላንን ያልተከተለ በመሆኑና በመኳንንቱና በመሳፍንቱ ግላዊ ፍላጐት ተወስኖ እንደቆየ አስታውሰዋል፡፡

‹‹የነገሥታቱ ዘመን ተጠናቆ የደርግ ዘመን ሲተካም ሁኔታዎች ባለመሻሻላቸው፣ ከተማዋ እንደስሟ አዲስ አበባ ሳትሆን ልማትና ዕድገት የሌላት፣ የኋሊዮሽ ጉዞ የጀመረች፣ ነዋሪዎቿ የትምህርት፣ የጤና፣ የንፁህ ውኃ አቅርቦትና የመሳሰሉትን አገልግሎቶች አጥተው በድህነት የሚማቅቁባት ከተማ እንደነበረች የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፤›› በማለት ከንቲባው ተናግረዋል፡፡ ባለፉት አሥር ዓመታት ግን በከተማዋ በሁሉም መስኮች የተገኘው ውጤትና እየታየ ያለው ለውጥ፣ ከመቶ ዓመታት በላይ በከተማዋ ተሠርተው ከነበሩት ልማቶች በብዙ እጥፍ እንደሚበልጥ አስረድተዋል፡፡

ከተማዋ አሁን ላላት ቅርፅና ደረጃ ከአንድ ክፍለ ዘመን ከሩብ በላይ ስትጓዝ፣ ባለፉት 125 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ብዙ ትውልዶች ተቀባብለው አስተዳድረዋታል ያሉት የትምህርት ሚኒስትርና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ናቸው፡፡ ‹‹በየምዕራፉ የነበሩት መንግሥታትም ከየራሳቸው ባህሪይ በመነጨ አካሄድ ከተማዋን መርተው አሻራቸውን በከተማዋ ላይ ትተዋል፤›› በማለት ገልጸዋል፡፡

አቶ ደመቀ አክለው፣ ‹‹ከተማዋ ለአገራዊና ለአኅጉራዊ እንቅስቃሴዎች ማዕከል በመሆን ለብዙ አሥርተ ዓመታት የቆየች ቢሆንም፣ ነዋሪዎቿ በቀጥታ ተሳትፈው የዕድገት ምህዋር ውስጥ ገብታ የዓለም አቀፍና የአፍሪካ መዲና ሆና የወጣችው ግን ካለፉት ሁለት አሥርተ ዓመታት ወዲህ ነው፤›› ብለዋል፡፡ 

የባቡር አገልግሎትን ጨምሮ ሰፋፊ የመሠረተ ልማት አውታሮችን መገንባት፣ የነዋሪዎችን የመኖሪያ ቤት እጥረት ማቃለል፣ የከተማዋን ጎስቋላ ገጽታ ሙሉ ለሙሉ መቀየርና በከተማዋ የተንሰራፋውን ኪራይ ሰብሳቢነትን መከላከል በከተማዋ ላይ በቀጣይነት በስፋት እንደሚሠራበት አቶ ኩማ ገልጸዋል፡፡

አዲስ አበባ በ1879 ዓ.ም. እንደተቆረቆረች የታሪክ ድርሳናት ይናገራሉ፡፡ በአሁኑ ጊዜም የአፍሪካ የዲፕሎማሲና የፖለቲካ ማዕከል ስትሆን፣ በርካታ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች መቀመጫ አድርገዋታል፡፡
Source: Reporter

No comments:

Post a Comment