Wednesday, October 24, 2012

የልጆቹን እናት በበርካታ ጥይቶች ደብድቦ ለገደለው ተጠርጣሪ ተመጣጣኝ ቅጣት ተጠየቀ

(Oct 24, 2012, በታምሩ ጽጌ, Addis Ababa)--ባለፈው ቅዳሜ ጥቅምት 10 ቀን 2005 ዓ.ም. ማለዳ ሁለት ሕፃናት ልጆቿን ወላጆቿ ቤት አድርሳ ወደ ሥራዋ በመሄድ ላይ የነበረችውን ወ/ሮ ፍሬሕይወት ታደሰን በመኪና አሳዶ በክላሽንኮቭ ጠመንጃ በርካታ ጥይቶችን በመተኮስ፣ ገድሏታል በተባለው ተጠርጣሪና የቀድሞ ባለቤቷ አቶ የወንድወሰን ይልማ ላይ ተመጣጣኝ ቅጣት እንዲጣል ቤተሰቦቿ ጠየቁ፡፡

በአሲድና በስለት የተጀመረው የሴት ልጆች ጥቃት ወደ ጦር መሣርያ መሸጋገሩን፣ በልጃቸው ላይ በጥይት እሩምተ የተፈጸመው ግን እስከዛሬ ከታየውና ከተሰማው የተለየና ጭካኔ የተሞላበትና የግፍ ግድያ በመሆኑ፣ ይህንን ድርጊት የሰማና የተመለከተ ኢትዮጵያዊ ሁሉ እንዲፋረድላቸው የጠየቁት የሟች ወላጆች፣ መንግሥት አፋጣኝና ተገቢ የሆነ የቅጣት ዕርምጃ እንዲወስድም ጠይቀዋል፡፡

ከሟች ጋር አብረው የነበሩትና በጥይት ፍንጥርጣሪ ተመትተው የተረፉት ወላጅ እናቷ ወ/ሮ ተናኘ ኃይለ ማርያም፣ ጥቅምት 10 ቀን 2005 ዓ.ም. በልጃቸው ላይ የተፈጸመውን የግድያ አፈጻጸም እንደገለጹት፣ ሟች ፍሬሕይወትና ተጠርጣሪው ገዳይ አቶ የወንድወሰን ከተለያዩ አንድ ዓመት ከስድስት ወራት ሆኗቸዋል፡፡ ፍቺው የተፈጸመው በፍርድ ቤት ነው፡፡ በትዳር በቆዩባቸው አራት ዓመታት ውስጥ የወለዷቸው የአራት ዓመት ሴትና የሁለት ዓመት ከስድስት ወራት ወንድ ልጆች አሏቸው፡፡ 
ፍቺው በፍርድ ቤት ሲፈጸም፣ ተጠርጣሪው በሳምንት ቅዳሜ ቅዳሜ ልጆቹን ወስዶ ካዝናና በኋላ ለእናታቸው እንዲያስረክብ ተወስኖ ነበር፡፡ በውሳኔው መሠረት ላለፉት አንድ ዓመት ከስድስት ወራት ይኼው ሲፈጸም ቆይቷል፡፡ ጥቅምት 10 ቀን 2005 ዓ.ም. ሟች በጠዋት ልጆቿን ወደ ቤተሰቦቿ ቤት ወስዳ ከእናቷ ጋር ጉዞዋን ወደ መሥርያ ቤቷ ማድረጓን ገልጸዋል፡፡

ከካዛንችስ መናኸሪያ ሆቴል ፊት ለፊት ከሚገኘው የወላጆቿ ቤት ተነስተው ዮርዳኖስ ሆቴል ፊት ለፊት ወደ ኦሊምፒያ የሚያሻግረው ድልድይ ላይ ሲደርሱ፣ ከኋላቸው ከፍተኛ የሆነ የተሽከርካሪ ጥሩንባ በመስማታቸው፣ ሟች ‹‹ምንድነው?›› ብላ በመኪናዋ ስፖኪዮ ስትመለከት ተጠርጣሪው መሆኑን ማወቋን የገለጹት እናቷ፣ ‹‹እሱ ነው›› በማለት ወደፊት እየፈጠነች ነድታ ደንበል ሲቲ ሴንተርን እንዳቋረጠች ፖሊሶች በማየቷ ስታቆም፣ ገዳይ እንደበረረ መጥቶ በመውረጃዋ በር በኩል መኪናውን በማስጠጋት የእሷ በር እንዳይከፈት ማድረጉን ተናግረዋል፡፡

እናቷ ባሉበት በር በኩል እንድትወጣ ቢስቧትም አሥራው የነበረው የአደጋ መከላከያ ቀበቶ ከነበረው ድንጋጤ ጋር ተዳምሮ አልፈታ በማለቱ፣ ተጠርጣሪው ክላንሽኮቭ ጠመንጃ በማውጣት ውስጡ ያሉ ጥይቶችን እንዳርከፈከፈባት አስታውቀዋል፡፡
ተጠርጣሪው አደጋ ያደረሰው በፍሬሕይወት ላይ ብቻ ሳይሆን በሌሎች በሁለት ግለሰቦች ላይ ጭምር መሆኑን የገለጹት ወ/ሮ ተናኘ፣ በተለይ አንዱ ተጐጂ በሰውነቱ ውስጥ ጥይቶች እንዳሉና እንዳልወጣለትም መስማታቸውን ተናግረዋል፡፡

‹‹እነዚህን ሁለት ጨቅላ ሕፃናት ለእኛ አዛውንት ወላጆቿ ጥላብን አለፈች፡፡ በዚህ ዕድሜያችን ምን እናድርጋቸው? ከእናታቸው ብዙ ነገር ለምደዋል፡፡ ገና ካሁኑ ትልቋ የእናቷን ፎቶግራፍ አቅፋ መተኛትና መተከዝ ጀምራለች፡፡ ወላድ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ይፍረደን፤›› ያሉት አባቷ አቶ ታደሰ ተፈራ፣ ፍሬሕይወት ሁለተኛ ልጃቸውና የ29 ዓመት ወጣት መሆኗን አስረድተዋል፡፡

ተጠርጣሪው ከተፋቱ ጊዜ ጀምሮ እንደሚገድላት ይዝት እንደነበርና ይኼንንም ለፖሊስ ማስመዝገባቸውን የገለጹት አቶ ታደሰ፣ የተናገረውን እንዲፈጽምና የልብ ልብ እንዲሰማው ያደረጉት ከዚህ ቀደም አሲድ የደፉ፣ በጩቤ የወጉና ያረዱ፣ ዓይን ያወጡና በሴቶች ላይ የተለያዩ ዘግናኝ ወንጀሎችን በፈጸሙ ወንጀለኞች ላይ የተላለፉት የቅጣት ውሳኔዎች መሆናቸውን በምሬት ተናግረዋል፡፡

ቻይና ውስጥ ጉቦ የተቀበለ ሰው በስቅላት ሲቀጣ፣ በኢትዮጵያ ግን በአሰቃቂ ሁኔታ ሕይወት ያጠፋ ከ20 ዓመታት በታች ቅጣት ተወስኖበት፣ በአመክሮና በተለያዩ አጋጣሚዎች ተለቆ እየኖረ መሆኑን የተናገሩት አቶ ታደሰ፣ በልጃቸው ላይ የደረሰው አሰቃቂ የግፍ ግድያ በተለይ በፖሊሶች ፊት መሆኑ፣ ሕጉ ምን ያህል እየላላ እንደሄደና ወንጀለኞች እየተበራከቱ መሆኑን የሚያሳይ ተግባር እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡

‹‹ዛሬ ወንጀለኞች እየተጠቀሙ ነው፤ የገደለም፣ የደፈረም ቅጣቱ ተመሳሳይ ሆኗል፤›› ያሉት የሟች አባት፣ በልጃቸው ላይ የደረሰው የግፍ ግድያ በማንም ላይ ተፈጽሞ የማያውቅ በመሆኑ መንግሥት ተመጣጣኝ ቅጣት በመስጠት የልጃቸውን ደም እንዲያወጣላቸው ጠይቀዋል፡፡

ወንጀል ፈጻሚዎች ወንጀል የሚፈጽሙት የሚደርስባቸውን ቅጣት በማሰብ ጥሩ ተከራካሪ ጠበቃ እንደሚያቆሙ፣ የሚወሰንባቸው ቅጣትም በአመክሮና በተለያዩ ምክንያቶች ተቀናንሶ እንደሚፈቱ በማሰብ መሆኑን የገለጹት አቶ ታደሰ፣ የወንጀል ሕጉ የሚያሳርፈው የቅጣት ውሳኔ ለወንጀል የሚገፋፋ በመሆኑ መሻሻልና መጠንከር እንዳለበትም አሳስበዋል፡፡

ሟችና ተጠርጣሪ በ1999 ዓ.ም. ተጋብተው እስከ 2003 ዓ.ም. ድረስ ሲኖሩ ስምምነት እንዳልነበራቸው፣ በተደጋጋሚ በሽምግልና ሲታረቁ እንደኖሩ፣ ተጠርጣሪው ፀባዩ ከመሻሻል የልቅ እየባሰበት ሄዶ አላስፈላጊ ደረጃ ላይ በመድረሱ፣ ለልጆቿ ደኅንነትና ለራሷም ስትል በመጨረሻ መፋታታቸውን የገለጹት አቶ ታደሰ፣ ፍርድ ቤት እንዲፋቱና ንብረታቸውን እንዲካፈሉ ከወሰነ በኋላ ‹‹ንብረት አልፈልግም፣ ለራሱ ይሁንለት፤›› ብላ ተከራይታ ልጆቿን እያሳደገች እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ሟች ፍሬሕይወት ቀደም ባሉት ዓመታት በክሊንተን ፋውንዴሽን ትሠራ እንደነበርና በአሁኑ ጊዜ ግን የራሷን ድርጅት ከፍታ እየሠራች እንደነበርም ታውቋል፡፡

ተጠርጣሪውን በቁጥጥር ሥር ያዋለው የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የሰው መግደል ወንጀልና ምርመራ ዲቪዚዮን፣ ሟች በስንት ጥይቶች ተመትታ እንደሞተች ለማረጋገጥ የአስከሬን ምርመራ ውጤት እየጠበቀ መሆኑን ገልጿል፡፡ ተጠርጣሪውን ፍርድ ቤት አቅርቦ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ በመጠየቅ በምርመራ ላይ መሆኑንም አስታውቋል፡፡ ተጠርጣሪው ግድያ ፈጽሞበታል የተባለውን ክላሽንኮቭ ጠመንጃም ከየት እንዳመጣውና ፈቃድ ያለው ወይም የሌለው ስለመሆኑ እያጣራ መሆኑንም አስረድቷል፡፡ በትዳር ውስጥ አለመግባባት ሲኖር በሽምግልናና በመሳሰሉ ሁኔታዎች አለመግባባትን መፍታት ወሳኝ መሆኑን የገለጸው ዲቪዚዮኑ፣ በትዕግስት ማጣት የሚፈጸም ወንጀል ትርፉ ፀፀትና ቤተሰብን መበተን ብቻ በመሆኑ ቆም ብሎ ማሰብ አስፈላጊና ጠቃሚ መሆኑን በመጠቆም መክሯል፡፡

ባለፈው እሑድ ጥቅምት 11 ቀን 2005 ዓ.ም. ‹‹የልጆቹን እናት በጥይት ደብድቦ ገድሏል የተባለው ተጠርጣሪ በቁጥጥር ሥር ዋለ›› በሚለው የዜና ዘገባችን ውስጥ ‹‹ሟች ሌላ ትዳር ይዛ አንድ ልጅ ወልዳለች፣ ንብረት ተከፋፍላለችና ተጠርጣሪው በልጆቹ ላይ አደጋ ሳያደርስ አይቀርም፤›› የዓይን እማኞች መናገራቸውን መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ነገር ግን ሟች አለማግባቷን፣ ንብረት አለመከፋፈሏንና በልጆቹም ላይ የደረሰ አደጋ አለመኖሩን ከቤተሰቦቿ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡
Source: Reporter   

No comments:

Post a Comment