Wednesday, September 05, 2012

የኢሲኤ ሠራተኛ ራሳቸውን ከፎቅ ወርውረው ገደሉ

(Sept 04, 2012, Reporter)--የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) ረዳት የፋይናንስ ሠራተኛ የነበሩት ወ/ት አልማዝ ልዑልሰገድ የተባሉ የ56 ዓመት የዕድሜ ባለፀጋ፣ ባልታወቀ ምክንያት ባለፈው ሰኞ ራሳቸውን ከኢሲኤ ስምንተኛ ፎቅ ወርውረው ገደሉ፡፡

የድርጅቱ ምንጮች እንደገለጹት፣ ለወትሮው ከመሥርያ ቤቱ ሠራተኞች ጋር መልካም ግንኙነት የነበራቸው ወ/ት አልማዝ ሰኞ ጠዋት ቢሮ ከገቡ በኋላ ‹‹መኖር አልፈልግም›› እያሉ በተደጋጋሚ መግለጻቸው የቢሮ ባልደረቦቻቸውን ያስደነገጠ ክስተት ነበር፡፡

ወ/ት አልማዝ ከወትሮው በተለየ ሁኔታ ሕይወት እንዳማረራቸው በመግለጽ መኖር እንደማይፈልጉ መናገራቸው ያስጨነቃቸው የቢሮ ባልደረቦቻቸው፣ ችግራቸውን እንዲነግሯቸው ቢጠይቋቸውም እሳቸው ለመግለጽ ፈቃደኛ አለመሆናቸው ታውቋል፡፡

ሟች የገጠማቸውን ችግር ለመናገር አለመፈለጋቸውን የተረዱት የቢሮ ሠራተኞች ‹‹ወደ ክሊኒክ እንውሰድሽ›› በሚል ሌላ መፍትሔ ቢያቀርቡም፣ የእሳቸውን ይሁንታ ለማግኘት አልቻሉም፡፡ ወ/ት አልማዝ ‹‹ወደ ክሊኒክ አልሄድም›› ቢሉም ባልደረቦቻቸው ዝም ብለው አልተቀመጡም፡፡ ወደ ክሊኒክ ሄደው ነርሶችን በማምጣት እንዲያነጋግሯቸው አድርገዋል፡፡ ወ/ት አልማዝን ለማነጋገር የመጡት ነርሶች ግን የገጠማቸው ምላሽ ተመሳሳይ ነው፡፡ ሟች ችግራቸውን ለማንም ለመግለጽ አልፈለጉም ነበር፡፡

ያልተጠበቀውና አሰቃቂው አደጋ የተከሰተው ከዚህ በኋላ ነው፡፡ ወደ ክሊኒክ እንሂድና እናነጋግርሽ በማለት በተደጋጋሚ ከነርሶች ለሚቀርብላቸው ጥያቄ የእምቢተኝነት ምላሽ የሰጡት ወ/ት አልማዝ፣ ባልተጠበቀ ሁኔታ ጫማቸውን አውልቀው ስምንተኛ ፎቅ የሚገኘውን የቢሮአቸውን መስኮት ከፍተው ራሳቸውን ወረወሩ፡፡ አዲሱንና አሮጌውን የኢሲኤ ሕንፃዎች በሚያገናኘው ሦስተኛ ፎቅ ላይ ባለው ድልድይ ላይ የተፈጠፈጡት ወ/ት አልማዝ፣ ሕይወታቸው ያለፈው ወዲያውኑ ነበር፡፡

ምንጮች እንደገለጹት፣ በስማቸው የተመዘገበ ቤትና መኪና የነበራቸውና በመሥርያ ቤታቸው ጥሩ ተከፋይ የነበሩት ወ/ሮ አልማዝ ትዳር አልመሠረቱም፤ ልጆችም አላፈሩም፡፡ ሰኞ ዕለት በሚኒልክ ሆስፒታል የወ/ት አልማዝ አስከሬን ምርመራ ከተደረገለት በኋላ፣ ለቡ አካባቢ በሚገኘው በቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ቀብራቸው የተፈጸመ መሆኑን ለመረዳት ችለናል፡፡
Source: Reporter

No comments:

Post a Comment