Friday, September 14, 2012

ኢትዮጵያውያን በአዲሱ ዓመት ለአገራቸው ዕድገት የጀመሩትን እንቅስቃሴ እንዲያጠናክሩ የሃይማኖት አባቶች አሳሰቡ

(ጳጉሜ 5/2004, (አዲስ አበባ, ኢዜአ))--ኢትዮጵያውያን በአዲሱ ዓመት ለአገራቸው ዕድገት የጀመሩትን እንቅስቃሴ በማዋል ለልማታቸው የሚያደርጉትን ጥረት እንዲያጠናክሩ የሃይማኖት አባቶች አሳሰቡ።

ብጹዕ አቡነ ናትናኤል
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ብጹዕ አቡነ ናትናኤልና የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳሳት ብፁዕ አቡነ ብርሃነየሱስ በየበኩላቸው ባስተላለፉት መልዕክት ዜጎች አዲሱን ዓመት ሲቀበሉ ለአገራቸው ልማትና ዕድገት የሚያደርጉትን ጥረት ለማጠናከር ቃል በመግባት መሆን ይገባዋል።

''የሰው ልጅ የኖረበት ዘመን ሁሉ የሥራና የታሪክ ዘመን ሆኖ ይታያል። ከዚህ አንጻር ሁሉም ኅብረተሰብ መልካም ታሪክን በማስመዝገብ በተሰለፈበት ዓላማ የሚጠበቅበትን ድርሻ ማበርከት ይኖርበታል'' ያሉት ብጹዕ አቡነ ናትናኤል፣ አዲሱ ዓመት የዘመን ለውጥ ብቻ ሳይሆን፤ አዲስ ሥራን የሚጀምርበት ሊሆን እንደሚገባው አመልክተዋል።

''ባለፈው ዘመን ልንሰራው የሚገባንን ሰርተን ከሆነ በአዲሱም ዘመን የበለጠ መልካም ሥራን መሥራት እንችላለን። ልንሰራው የሚገባንን ሳንሰራ እንዲሁ ጊዜውን በቸልተኝነት አሳልፈነው ከሆነ ደግሞ የዘመኑ መለወጥ ብቻ ፋይዳ የለውም።'' ብለዋል። ለአገር ልማትና ለወገን ዕድገት የሚሆን ሥራን በታሪክ አስመዝግቦ ማለፍ ታላቅ ተግባር መሆኑንም አቡነ ናትናኤል አስረድተዋል። አዲሱ ዓመት ሲከበር በተለያየ ምክንያት ወላጆቻቸውን ያጡ፣ ጧሪ የሌላቸውን አረጋውያን፣ ለችግርና ለደዌ የተጋለጡትን ወገኖች መርዳት እንደሚያስፈልግም ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ አሳስበዋል።

ኢትዮጵያውያን መንግሥት አገሪቱን ለማሳደግ የጀመራቸውን የልማት ሥራዎች ለመደገፍ እጅ ለእጅ ተያይዘው መንቀሳቀስ እንደሚገባቸው አቡነ ብርሃነየሱስ አስገንዝበዋል። በታታሪነት ከተቀጠለ በድህነት ላይ በአጭር ጊዜ ድልን መቀዳጀት እንደሚቻል ተናግረዋል። አገሪቱ በዓለም የታወቀችበትን የመቻቻልና የመከባበር ባህል በማስጠበቅ ለመጪው ትውልድ እንዲተላለፍ ማድረግ እንደሚያሻ ሊቀ ጳጳሱ አሳስበዋል።

''በአገራችን እየተካሄደ ያለው የሰው ልጆች ሕገ ወጥ ዝውውርን በተመለከተ መንግሥት ትኩረት ሰጥቶ የተለያዩ ኮሚቴዎችን በማቋቋም ለመታደግ እየሰራ ያለውን ሥራ በማድነቅ ይህንንም በማጠናከር የአገርን ገፅታ ከመለወጥ አንጻር ዜጎች በአገራቸው ሰርተው የመኖር ባህልን እንዲያዳብሩ እናስገነዝባለን'' ብለዋል። ኅብረተሰቡ የዘመን መለወጫ በዓልን ሲያከብር በችግር ላይ የሚገኙ ወገኖቹን በማሰብና የአቅሙን መለገስ እንደሚገባውም አቡነ ብርሃነየሱስ መግለጻቸውን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዘገባ አስታውቋል።
ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት

No comments:

Post a Comment