Saturday, September 01, 2012

በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ ለመገኘት የበርካታ አገራት መሪዎች አዲስ አበባ እየገቡ ነው

(አዲስ አበባ ነሃሴ 26/2004)--ነገ በሚካሄደው የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ ለመገኘት የበርካታ አገራት ፕሬዝዳንቶች፣ጠቅላይ ሚኒስትሮችና የልዑካን ቡድን አባላት አዲስ አበባ መግባታቸውን ቀጥለዋል። 

የቀብር ሥነ ሥርዓቱ ላይ ለመገኘት ዛሬ ማምሻውን አዲስ አበባ ከገቡት መሪዎች መካከል የኬንያው ፣የዩጋንዳ፣የናይጄሪያ ፣የሶማሊያ ፣የሱዳን፣የሩዋንዳ ፕሬዚዳንቶች፣የጋቦንና የናሚቢያ ጠቅላይ ሚኒስትሮች፣የጋና ምክትል ፕሬዝዳንት፣የአልጄሪያና የየመን ሸንጎ ምክር ቤት አፈጉባኤዎች፣የናይጄሪያና የደቡብ አፍሪካ የቀድሞ ፕሬዚዳንቶች፣የጣሊያን ልኡካን ቡድን አባላትና እውቁ የናይጄሪያ ባለሃብት ሚስተር አሊኮ ዳንጎቴ አዲስ አበባ ገብተዋል።

 መሪዎቹና የልኡካን ቡድኑ አባላት አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት ሲደርሱ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መኮነን ማንያዝዋል እና የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር አብዱልፈታህ አብዱላሂ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ ዲፕሎማቶች ተቀብለዋቸዋል።

የሱዳኑ ፕሬዚዳንት ኦማር ሃሰን አልበሽር ሱዳናውያን የሰላምና የልማት ወዳጅ የሆኑትን ጠንካራ ሰው በማጣታቸው ከፍተኛ ሃዘን እንደተሰማቸው ገልጸዋል። አቶ መለስ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካም ታላቅ ተስፋና የለውጥ ራዕይ ተደርገው የሚወሰዱ እንደነበሩ ጠቁመዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ የቅርብ ወዳጅ የሆኑት የዩጋንዳው ፕሬዚዳንት ዩቬሪ ሙሰቬኒ አቶ መለስ ለኢትዮጵያ ህዳሴና አገሪቱን ዘመናዊ በማድረግ፣ለአፍሪካ አህጉር መጠናከር ተጠቃሽ ጥረቶችን ያደረጉ መሪ እንደነበሩ ተናግረዋል።

አቶ መለስ በምስራቅ አፍሪካ እና በአፍሪካ ቀንድ መረጋጋትና ሰላም ጠንክረው የታገሉ ሰው እንደነበሩና እርሳቸው የጀመሩትን ጥረት አገራቸው ትገፋበታለች ብለዋል። የናይጄሪያው ፕሬዚዳንት ጉድላከ ጆናታን በበኩላቸው የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ህልፈት ለሁሉም አፍሪካዊ ታላቅ ድንጋጤ መሆኑን ተናግረዋል።

አቶ መለስ በስልጣን ዘመናቸው አፍሪካ በኢኮኖሚና በማህበራዊ መስኮች ጠንካራ አንድነት እንዲኖራት ያራምዱት የነበረውን ቁርጠኛ አቋም ሁልጊዜም እንደሚያስታውሱት ገልጸዋል። የሶማሊያው የሽግግር መንግስት ፕሬዚዳንት ሼክ ሼሪፍ ሼህ አህመድ የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ደንገተኛ ህልፈተ ህይወት ሲሰሙ እጅጉን እንዳስደነገጣቸው ጠቅሰዋል። ሼክ ሸሪፍ እንዳሉት የሶማሊያ ህዝብ አስቸጋሪ ሁኔታ በገጠመው ወቅት ከሁሉም ቀድመው የደረሱትና ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን ባበረከቱት አስተዋጽኦ በሶማሊያ የሰላም አባት እስከ መባል የደረሱ መሪ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

የጋቦን ጠቅላይ ሚኒስትር ራይሞንድ ዶንግ ሲማ በበኩላቸው የጋቦን መንግስትና ህዝብ የአቶ መለስን ድንገተኛ ሞት የሰሙት በከፍተኛ ድንጋጤና ሀዘን መሆኑን ገልጸዋል። አቶ መለስ የጋቦን ህዝብና መንግስት የቅርብ ወዳጅና ጠንካራ አጋር እንደነበሩና የሁለቱ አገራት የሁለትዮሽ ግንኙነትም ከአዲሱ አመራር ጋር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። አቶ መለስ በአየር ንብረት ለውጥና በሰላምና ጸጥታ ጉዳዮች የአፍሪካን ድምጽ በአለም መድረክ እንዲሰማ ሰፊ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውንም አስታውሰዋል።

የናሚቢያ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሐስ አንጉላ በበኩላቸው አቶ መለስ በኢትዮጵያ ያስመዘገቡት ስኬታማ የኢኮኖሚ ጉዞ በአፍሪካ መንግስታት ዘንድ እንደ ሞዴል የሚቆጠር መሆኑን ገልጸዋል። የአቶ መለስን አመራር የሚረከበው ቀጣዩ አመራርም ፈለጋቸውን ተከትሎ የአገሪቱን የስኬት ጉዞ ያፋጥናሉ የሚል ጽኑ እምነት እንዳላቸው ገልጸዋል።

የጋናው ምክትል ፕሬዝዳንት ክዌሲ አሚሳህ አርተር በበኩላቸው አቶ መለስ አፍሪካ በሰላምና ጸጥታ፣በኢኮኖሚ፣በማህበራዊ መስኮች ውጤት እንዲመዘገብ ያደረጉት አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው። የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዝዳንት ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ለአፍሪካ ልማት፣ሠላምና መረጋጋት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክቱ መሆናቸውን ገልጸው መላው የአፍሪካ ሕዝብና መንግስት ዘወትር ሲያስታውሳቸው ይኖራል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
Source: ENA

Related topics:
በመለስ ሽኝት ዋዜማ 
ባራክ ኦባማ በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሥርዓተ ቀብር የሚገኝ ቡድን እንደሚልኩ አስታወቁ 
በደቡብ አፍሪካ የሚገኙ ኤርትራውያን የኅዘን መግለጫ አስተላለፉ 
የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ስርዓተ ቀብር ዛሬ ተፈፀመ 
ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ አረፉ  

No comments:

Post a Comment