Sunday, August 05, 2012

የውጭ ኢንቨስተሮች በአደንዛዥ ዕፅ ንግድ ተጠርጥረው ክስ ተመሠረተባቸው

(Aug 05, 2012, Reporter)--ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኤጀንሲ ለተለያዩ የሥራ ዘርፎች  የኢንቨስትመንት ፈቃድ ከወሰዱ በኋላ፣ አደንዛዥ ዕፅ በማምረት፣ በማዘጋጀትና ወደ ተለያዩ የዓለም አገሮች ሲልኩ ነበር የተባሉ የጃማይካና የኔዘርላንድ ዜጎች፣ ከኢትዮጵያውያን ተባባሪዎቻቸው ጋር እጅ ከፍንጅ ተይዘው ክስ ተመሠረተባቸው፡፡

የፌደራል ከፍተኛ ዓቃቤ ሕግ በዋና ወንጀል አድራጊነት ፈርጆ ክስ የመሠረተባቸው፣ ሚስተር ሊፊታ ንክሩማን (ጀማይካዊ)፣ አልቤርቶ ራሚሼል ቅጽል ስም ሰለሞን (ኔዘርላንዳዊ)፣ ዮናስ ኪሮስ፣ አልአዛር ተስፋ እዝጊነ መንግስቱ ተካ  የተባሉ ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡ ያልተያዙና ተባባሪ ናቸው የተባሉ  ተጠርጣሪዎች ሚስተር ብራውን ዱዳ፣ ሚስተር ሮበን፣ ሚስተር መሐመድ፣ ሚስር ሔኖክ ወይንጀምና ሚስተር ኤሪክ ናቸው፡፡

በ1999 ዓ.ም. ወደ ኢትዮጵያ መግባቱንና ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኤጀንሲ በምግብ ማቀነባባሪያ የሥራ ዘርፍ ፈቃድ አውጥቶ፣ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ አርሲ ዞን ሻሸመኔ ከተማ ፋብሪካ መገንባቱ የተገለጸው ጀማይካዊው ሚስተር ሊፊታ ንክሩማን፣ ዋናው የወንጀሉ አቀነባባሪ መሆኑ በክሱ ተጠቁሟል፡፡

ግለሰቡ የሰው ልጆችን ሱስ በማስያዝ ለተለያዩ የወንጀል ድርጊቶች የመገፋፋትና የማነሳሳት ባህሪ ያለውንና በልዩ ፈቃድ ካልተፈቀደ በስተቀር እንዳይመረት፣ እንዳይሸጥ፣ እንዳይዘዋወርና ጥቅም ላይ እንዳይውል በሕግ የተከለከተውን ካናቢስ የተባለውን አደንዛዝ ዕፅ ኢትዮጵያ ወስጥ ሲያመርት ነበር፡፡

ዕፁን ካመረቱ በኋላ በፖስታ ቤት ከኩል በተለያዩ ባህላዊ ዕቃዎች፣ ልብሶች፣ ሽሮና በርበሬ  ውስጥ በመደበቅ በተደጋጋሚ ሲልክ ተገኝቶ ተከሶ እንደነበር ተገልጻል፡፡ ከጥቅምት ወር 2004 ዓ.ም ጀምሮ በውል በማይታወቅ ጊዜ ውስጥ ከ200 ኪሎ ግራም በላይ ዕፅ ሳይፈተሽ ወደ እንግሊዝ አገር ለመላክ ከአየር መንገድ ደኅንነቶች ጋር በ300 ሺሕ ብር ከተዋዋለና 100 ሺሕ ብር ቅድሚያ ከሰጠ በኋላ፣ ፍተሻ ላይ እጅ ከፍንጅ ዕፁ በመያዙ ግለሰቡ ቢሰወርም ኬንያ ላይ መያዙን ክሱ ያስረዳል፡፡

ከኢንቨስትመንት ኤጀንሲ በአልባሳት ዲዛይንና የልብስ ስፌት የሥራ ዘርፎች ፈቃድ  የወሰደው ኔዘርላንዳዊው አልቤርቶ ራሚሼል የተባለው ተከሳሽ ደግሞ፣ አየር መንገድ ሠራተኞች  ጉቦ በመስጠት 50 ኪሎ ግራም የሚጠጋ ካናቢስ አደንዛዥ ዕፅ፣ በተደጋጋሚ ወደ እንግሊዝ መላኩ በክሱ ተጠቅሷል፡፡

ከግለሰቡ ጋር  ዮናስ ኪሮስ የተባለው ተከሳሽ ካናቢሱን ከሻሸመኔ እየተቀበለ   በፖስታ ቤት ሠራተኞች ትብብር ወደ የእንግሊዝ ከተማ ወደሆነችው በርሚንግሀምና ሌሎች አገሮች በተከታታይ የላከ መሆኑም በክሱ ተጠቁሟል፡፡ በኢትዮጵያ አየር መንገድ በኩል ወደ ውጭ ለመላክ ለሠራተኞቹ 100 ሺሕ ብር ጉቦ ሲሰጥ እጅ ከፍንጅ መያዙም በክስ ቻርጁ ስፍሯል፡፡

ወደ185 ኪሎ ግራም ካናቢስ አደንዛዥ ዕፅ በኤምሬትስ አየር መንገድ በኩል ለመላክ ሲሞክር በተደረገ ፍተሸ እጅ ከፍንጅ የተያዘው አራተኛው ተከሳሽ አልአዛር ተስፋ እግዚ ሲሆን፣ በባህል ዕቃ ውስጥ በካርቶን አድርጎ ለማስወጣት ሲሞክር መያዙን የክስ ቻርጁ ያብራራል፡፡

የተከሳሾቹ ጠበቆች ደንበኞቻቸው በዋስ እንዲለቀቁ ቢጠይቁም፣ ቀደም ባለና  በተመሳሳይ ክስ በጠቅላይ ፍርድ ቤት ዋስትና የተከለከሉ በመሆኑ ዋስትናው አልተፈቀደላቸውም፡፡  ዓቃቤ ሕግ የሰዎች ምስክሮቹን ህዳር 6 ቀን 2005 ዓ.ም አቅርቦ እንዲያሰማና ተከሳሾቹም ማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ትዕዛዝ ተሰጥቶ ችሎቱ አብቅቷል፡፡
Source: Reporter

No comments:

Post a Comment