Sunday, March 18, 2012

በሊባኖስ በሞተችው ኢትዮጵያዊት አሠሪ ላይ ክስ ተመሠረተ

(Mar 18, 2012, Reporter)--በሊባኖሳዊ አሠሪዋ መሬት ለመሬት ስትጎተት፣ ስትንገላታና ስትደበደብ በሊባኖሱ ኤልቢሲ ቴሌቪዥን ጣቢያ የታየችው ኢትዮጵያዊቷ ዓለም ደቻሳ ደሲሳ ራሷን እንዳጠፋች በመገለጹ፣ ራሷን በመግደሏ ላይ ጥርጣሬ አለን የሚለው በሊባኖስ የኢትዮጵያ ቆንስላ ጽሕፈት ቤት በአሠሪዋ ላይ ክስ በመመሥረት የአሟሟቷ ሁኔታ እንዲጣራለት ጠይቋል፡፡

ከዚህ በፊት በሠራተኞቻቸው ላይ በደል የፈጸሙ አሠሪዎች የተቀጡት የ15 ቀናትና የአንድ ወር እስር ብቻ ነው፡፡

በሊባኖስ የኢትዮጵያ ቆንስላ ኃላፊ አቶ አሳምነው ደበሌ ቦንሳ በስልክ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ቅዳሜ መጋቢት 1 ቀን 2004 ዓ.ም. እሳቸውን ጨምሮ ሌሎችም የተኛችበት ሳይኪያትሪክ ዲ.ላ. ክሮክሲ ሆስፒታል ድረስ በመሄድ ጠይቀዋታል፡፡ ሰኞ መጋቢት 3 ቀን 2004 ዓ.ም. ደግሞ ሌሎች ኢትዮጵያውያን ሄደው አይተዋት ሰላም መሆኗንና የአዕምሮዋ ሁኔታ የተረጋጋ እንደነበረ ነግረዋቸዋል፡፡ ረቡዕ መጋቢት 5 ቀን 2004 ዓ.ም. አሠሪዋ የፈጸመባትን በደል በተመለከተ ጉዳዩን ከያዘው ፖሊስ ጋር ስለክሱ ለመነጋገር ሲሄዱ፣ ፖሊሱ ‹‹ልጇቷ እኮ ሕይወቷ አልፏል!›› በማለቱ ወዲያው ወደ አዕምሮ ሕክምና ሆስፒታሉ ሄደው፣ ሕይወቷ ማለፉን ከሕክምና ባለሙያዎች አረጋግጠዋል፡፡

‹‹የሆስፒታሉን አስተዳደርና ሕክምና የሚያደርጉላትን ዶክተር አነጋገርናቸው የሆነው ምንድነው? ከዚህ ቀደም በሆስፒታሉ የገቡ ኢትዮጵያውያን ታክመው ድነው ወጥተዋል፡፡ በቅርብ ቀን ሆስፒታል የገባችው ዓለም ደቻሳ ደግሞ ሞታለች ተብሏል ብለን ጠየቅን፤›› የሚሉት አቶ አሳምነው፣ ከሕክምና ባለሙያዎቹ ያገኙት መልስ፣ ‹‹በመልካም ሁኔታ ላይ ስለሆንሽ ከሆስፒታል ወጥተሽ አገርሽ እንድትመለሽ ይደረጋል ብለን ነግረናት ነበር፡፡ በጥሩ ሁኔታ ላይም ነበረች፡፡ ማክሰኞ ለረቡዕ አጥቢያ የምትከታተላት ነርስ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ተኝታ አይታታለች፡፡ 11 ሰዓት ላይም ተኝታ ነበር፡፡ ለሦስተኛ ጊዜ በ12 ሰዓት ስትጎበኛት ለአየር ማስገቢያ በተከፈተ ኮሪደር ላይ አንሶላ ቀዳ ራሷን አጥፍታ ተገኘች፤› የሚል መልስ እንደተሰጣቸው ተናግረዋል፡፡

አስከሬኗን አይተው ባያረጋግጡም ስለ መሞቷ እርግጠኛ መሆናቸውንም እንደነገሯቸው አቶ አሳምነው ገልጸዋል፡፡ ራሷን ማጥፋትና አለማጥፋቷን በሚመለከት የአሟሟቷ ሁኔታ ላይ ጥርጣሬ ስላላቸው ምርመራ እንዲደረግ ጠይቀው ውጤቱን እየተጠባበቁ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ ‹‹የሰማነው ረቡዕ መጋቢት 5 ቀን 2004 ዓ.ም. በአምስት ሰዓት ላይ ሲሆን፣ የሞተችው ማክሰኞ ለረቡዕ አጥቢያ ከንጋቱ 12 ሰዓት ላይ ነው፤›› የሚሉት አቶ አሳምነው፣ ክስ መመሥረታቸውን ተናግረዋል፡፡ በአሟሟቷ ላይ ጥርጣሬ እንዳላቸው ሲገልጹም፣ ‹‹ሌሎች በሆስፒታሉ የሚታከሙ ሁለት ኢትዮጵያውያን አሉን፡፡ በሌላ በኩል የአዕምሮ ሕክምና የሚሰጥ ሆስፒታል ውስጥ ታካሚ ራሱን እስኪያጠፋ ዕድል የሚሰጥ አሠራር የሌለና ጥበቃውም የተጠናከረ ነው፡፡ ጥንቃቄና ክትትል ያለበት ስለሆነ እንዴት ራሷን ልታጠፋ ቻለች የሚለውን እንዲጣራ እያደረግን ነው፤›› ብለዋል፡፡

የአዕምሮ ችግር አለባት የተባለውን ማረጋገጣቸውን በተመለከተም በሕክምና ችግሩ አለባት ተብሎ ሆስፒታል መግባቷን ተናግረዋል፡፡ ዓለምን ጠይቀዋት እንደተረዱትም፣ ሊባኖስ የገባችው ከሁለት ወራት በፊት ነው፡፡ አገባቧ በሕገወጥ መንገድ ቢሆንም በሕገወጥ መንገድ እንደገባች አታውቅም፡፡ ኢትዮጵያ ወደ ሊባኖስ ለቤት ሠራተኝነት የሚደረገውን የሥራ ጉዞ እንዳገደችም መረጃው የላትም፡፡ በመሆኑም ሊባኖስ የገባችው ከሰው ገንዘብ ተበድራ ሲሆን፣ ዓላማዋ ደግሞ ሠርታ ብድሯን ለመክፈልና ልጆቿን ለማሳደግ ነበር፡፡ ሊባኖስ የገባችው በሕገወጥ መንገድ መሆኑን ስትገነዘብ ግን አዕምሮዋ ተነካ፡፡ ተበሳጨች፡፡ ሆኖም ያለባት ጭንቀት እንጂ ሙሉ ለሙሉ የአዕምሮ ህመም አልነበረም ብለዋል፡፡

የ33 ዓመቷ ዓለም ደቻሳ ደሲሳ የቡራዩ ከተማ ነዋሪ እንደሆነች፣ ከባሏ መፋታትዋንና በዚህም ብስጭት እንዳለባት ሆስፒታል ሆና በጎበኟት ወቅት እንደነገረቻቸው አስረድተዋል፡፡ በእነሱ በኩልም መጀመርያ ጤንነት እንደሚቀድም፣ በማስከተል ደግሞ ገንዘቡን ልታገኝ እንደምትችል አሳምነዋት ደህና ሆና እንደነበር ገልጸዋል፡፡

በርካታ ኢትዮጵያውያት ብዙ በደሎች ይፈጸሙባቸዋል፤ በዓለም ላይ የድብደባና የማንገላታቱ ጥቃት የተፈጸመው የኢትዮጵያ ቆንስላ ጽሕፈት ቤት ፊት ለፊት ነው፤ እናንተ አላያችሁም ነበር ወይ? በማለት ለአቶ አሳምነው ጥያቄ አንስተን ነበር፡፡ በቆንስላነት ከተሾሙ ሦስት ዓመታትን ያስቆጠሩት አቶ አሳምነው እንደሚሉት፣ ከጅምሩ አንሥቶ ኢትዮጵያውያት በሕገወጥ መንገድ እንዳይመጡ እያስተማሩና እየረዷቸው ነው፡፡ በሕገወጥ መንገድ የሚመጡትና ችግር ውስጥ የተዘፈቁትም ቁጥራቸው ቀላል አይደለም፡፡ በየቦታው መደፈርን ጨምሮ በርካታ በደሎች አሉ፡፡ የዓለም ጉዳይ ይፋ የወጣው በአጋጣሚ ሚዲያ ስላገኘው ነው፡፡ የዓለምን ጉዳይ በተመለከተም አሠሪዋ ቆንስላው ጽሕፈት ቤት አምጥቷት አገሬ እሄዳለሁ እያለችው እንደሆነ ሲነግራቸው መብቷ ነው ብለው መመለሳቸውን፣ ከዚያም ራሴንም አጠፋለሁ እያለች ነው በማለቱ እንደዚህ ከሆነ የማሳከም ግዴታ ስላለብህ ሆስፒታል ውሰዳት ብለውት ተስማምተው ከጽሕፈት ቤቱ ከወጡ በኋላ ውጭ ሲደርሱ መኪና ውስጥ ግቢ አትግቢ በሚል እንግልት፣ ድብደባና ጉተታ በዓለም ላይ መፈጸሙን ገልጸዋል፡፡

አቶ አሳምነው እንደሚሉት፣ ግብግቡ ሲፈጠር ከጽሕፈት ቤታቸው ወጥተው ልጅቷን አስጥለዋል፡፡ ፖሊስ ጠርተውም አሠሪዋ  በቁጥጥር ሥር እንዲውል፣ እሷም ሆስፒታል እንድትሄድ አስደርገዋል፡፡ ሆኖም የፖሊሱም ሆነ የእሳቸው ተሳትፎ ሳይካተት ልጅቷ ስትደባደብና በግዳጅ መኪና ውስጥ ስትገባ ያለው ምስል ብቻ በሚዲያ ተለቋል፡፡

በቆንስላው በኩል የአቅማቸውን ያህል እየሠሩ መሆኑን፣ ከዚህ ቀደም 300 ሰዎች ምሕረት ተደርጎላቸው ወደ ኢትዮጵያ እንደተመለሱ በመግለጽ፣ የቆንስላ ጽሕፈት ቤቱ ለዜጎቹ ትኩረት እንዳልሰጠ ተደርጎ የሚፈረጀው ትክክል እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡ በጽሕፈት ቤቱ በኩል ዜጎችን ከገቡበት ችግር ለማውጣት እየተሠራ መሆኑንና  በሥራቸው በብዛት የተጠመዱትም ኢትዮጵያውያኑ ሲቸገሩ በመርዳት፣ አገራቸው እንዲመለሱ በማድረግ ላይ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

በቅርብ ቀን ከሐዲያ የመጣችና ከሐዲያ ቋንቋ በስተቀር መግባባት የማትችል ልጅ ማግኘታቸውን፣ በአስተርጓሚ በኩል እንደተረዱት ልጅቷ ደቡብ አፍሪካ እንዳለች የምታውቅ መሆኗን የሚገልጹት አቶ አሳምነው፣ የአዕምሮ ጭንቀት ስለነበረባት ሆስፒታል እንድትገባ ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡ ከሐውዜን (ትግራይ) የመጣችም እንዲሁ የቋንቋው ተናጋሪ ፈልገው እንዳነጋገሯትና በአጠቃላይም በሊባኖስ ያለው ችግር በጣም አስከፊ ገጽታ ያለው መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ይህንን ለማቃለል ዜጎች በሕጋዊ መንገድ እንዲገቡ፣ ዕድሜያቸውና የትምህርታቸው ሁኔታ ተጠንቶ በሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር በኩል ብቻ ሕጋዊ ሆነው የሚመጡበትን ፕሮፖዛል አቅርበውም እንዳልተቀበሏቸው ገልጸዋል፡፡

እገዳው ቢኖርም ኢትዮጵያውያኑ ሕገወጥ ሆነው ወደ ሊባኖስ መግባታቸው ስላልቀረ፣ በኢትዮጵያ ለሁሉም ዜጋ የሥራ ዕድል መፍጠር እስከሚቻል ድረስ በሕጋዊ መንገድ የሚመጡበትን ሁኔታ ለማመቻቸት እየሠሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባገኘነው መረጃ መሠረት፣ በቤይሩት በአጠቃላይ ሕጋዊ የሆኑ ኢትዮጵያዊ የቤት ሠራተኞች የሉም፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት የዜጎችን መብት የሚያስጠብቅ የጋራ የሥራ ስምምነት ላይ ካልተደረሰ ኢትዮጵያውያን ወደ ቤይሩት እንዳይሄዱ እገዳ ከጣለ ከሦስት ዓመታት በላይ ተቆጥረዋል፡፡ ይህም ሆኖ ግን ቀደም ባሉት ጊዜያት በየመን በኩል አሁን ደግሞ በሱዳን ወደ ቤይሩት የሚጓዙ ሴቶች ቁጥር በጣም ጨምሯል፡፡

እገዳው ከመጣሉ በፊት ሕጋዊ ሆነው ወደ ቤይሩት የገቡ ኢትዮጵያውያን ጊዜያቸውን ሲጨርሱ ወደ አገራቸው መመለስ ሲገባቸው ባለመመለሳቸው ሕገወጥ ሆነዋል፡፡ ኢትዮጵያ ዜጓቿ ወደ ሊባኖስ እንዳይሄዱ እገዳ ከጣለች ወዲህ የሄዱት በሙሉ ደግሞ በሕገወጥ መንገድ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ፡፡

በአሁኑ ወቅት ከኢትዮጵያ ጋር የዜጎችን መብትና ጥቅም የሚያስጠብቅ የጋራ የሥራ ስምምነት ተፈራርማ የምትገኝ አገር ኩዌት ብቻ ናት፡፡ የሳዑዲ ዓረቢያ ደግሞ በሒደት ላይ ይገኛል፡፡ በሊባኖስ ከ60 እስከ 70 ሺሕ የሚደርሱ ኢትዮጱውያን ይኖራሉ ተብሎ እንደሚገመት አቶ አሳምነው ገልጸዋል፡፡
Source: Reporter

No comments:

Post a Comment