Wednesday, April 05, 2017

ኢትዮጵያ በላሊበላ ተራራዎች ላይ ሳተላይትን በማምጠቅ ከአፍሪካ ከቀዳሚዎቹ ልትቀላቀል ነው

(Apr 05, 2017,  (አዲስ አበባ ))--ከባህር ጠለል በላይ 2 ሺህ 500 ሜትር የሚሆነው ታሪካዊው የላሊበላ ሰንሰለታማ ተራራዎች በአለም ለሳተላይት ማጠቂያነት ተመራጭ ከሆኑት ቺሊና ሀዋይ ማዕከላት የማይተናነስ አቅም እንዳላቸው ዘ ኢኮኖሚስት የተሰኘው ድረ ገፅ በዘገባው ይዞ ወጥቷል።  በቀጣይም ዘርፉን ለማልማት ኢትዮጵያ የራሷን የጠፈር ሳተላይት ለማምጠቅ እየሰራች መሆኑን አምልክቷል፡፡

በሚቀጥሉት 5 ዓመታት ውስጥም ኢትዮጵያዊ  ይዘት ያላት ሳተላይት በቻይና ተገንብታ ኢትዮጵያ ወደ ጠፈር ለማምጠቅ እየሰራች መሆኑን ድረ-ገፁ አስታውሷል፡፡ የሳተላይቱ ሞዴል የተቀረፀውም ሀገሪቱ በጠየቀችው መስፈርት እንደሆነና የሰብል ምርት፣ የአየር ሁኔታን እንዲሁም ሌሎች መረጃዎችን ለማሰባሰብ ጥቅም ላይ እንደሚውል ተመልክቷል፡፡

ሀገሪቱ የራሷ ሳተላይት ሲኖራትም በዘርፉ የውጭ ጥገኝነቷን እንድትቀንስ ያግዛልም ነው የተባለው፡፡  ኢትዮጵያ የራሷን ሳተላይቶች በጠፈር ምዕዋር ላይ ስታስቀምጥ በአፍሪካ ወደ ጠፈር ሳተላይት ካመጠቁ ጥቂት ሀገራት ተርታ እንደምትሰለፍ ተነግሯል፡፡

በአፍሪካ ናይጄሪያ፣ ደቡብ አፍሪካና ግብጽ በጠፈር ሳተላይት ያላቸው ሀገሮች ሲሆኑ ኬንያ፣ አንጎላና ጋና ደግሞ በዘርፉ ልማት ለመቀላቀል ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው ዘ ኢኮኖሚስት ጠቁሟል፡፡ የዘርፉ ልማት ለሀገሪቷ አያሌ ፋይዳ እንዳለው ይታመናል፡፡ ከዚህም ውስጥ የሀገሪቱን ማስተር ፕላን በመቅረጽ የመሬት ይገባኛል ግጭቶችን ለመፍታትና የግብርና ምርታማነትን ለማረጋገጥ ይጠቅማል ተብሏል፡፡

የከተሞችን እድገት ለማሻሻልና የኢንዱስትሪ ልማትን ለማፋጠን አገሪቱ ሳተላይት ማምጠቋ እንደሚጠቅማት ተመልክቷል። ይሁንጂ ቴክኖሎጂው የሚጠይቀው የሀብት መጠን ከፍተኛ  በመሆኑ እንደኢትዮጵያ ላለ ታዳጊ  አገር ብዙ ወጪ ሊያስወጣት ይችላል ብሏል ዘግባው።
ኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን

No comments:

Post a Comment