Sunday, April 12, 2015

በአሰልጣኝ ማሪያኖ ባሬቶ ላይ ፌዴሬሽኑ ዝምታን ለምን መረጠ?

(ሚያዚያ 3/2007, (አዲስ አበባ))--የሰሞኑን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝን በተመለከተ እየሰማን ያለነው ሁላችንንም ውዥንብር ውስጥ እየከተተ ነው። በተለያዩ መገናኛ ብዙሃንና የማህበረሰብ ድረ-ገፆች አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ከአሰልጣኝነታቸው መሰናበታቸውን ከሰማን ድፍን አንድ ሳምንት ሊሆነን ነው። ይህን ዜና የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ብቻም ሳይሆኑ እንደ ሱፐር ስፖርት ዶት ኮም ያሉ ድረ-ገፆችም አናፍሰውታል። እርግጥ ነው ዜናውን እየሰማን የምንገኘው ታማኝ ከሆኑም ካልሆኑም የመረጃ ምንጮች ሊሆን ይችላል።

ዜናውን ማንንም ከምንም ተነስቶ ሊነዛው ይችላልና ለስፖርት ቤተሰቡ ታማኝ መረጃ የሚያቀብሉ በርካታ የአገራችን መገናኛ ብዙሃን ጉዳዩን ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለማጣራት በርካታ ሙከራዎችን ለቀናት አድርገን ጠብ ያለ ምላሽ ግን ማግኘት አልተቻለም። አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ከአሰልጣኝነታቸው እንዳልተሰናበቱና ለትንሳዔ በዓል ወደ አገራቸው እንደገቡም የሚናገሩ ምንጮች አልጠፉም።ፌዴሬሽኑ በአሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶ ምትክ ወደ አገር ውስጥ አሰልጣኞች ፊቱን መመለሱም እየተነገረ ነው። የቀድሞው የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው፤ ውበቱ አባተ፤ ፀጋዬ ኪዳነ ማርያምና ዮሐንስ ሳህሌ እጩዎች እንደሆኑም ይወራል።

የቀድሞውን የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ አቶ ሰውነት ቢሻውን በዚህ ጉዳይ ላይ አንድ የኢትዮ ፉትቦል ጋዜጠኛ አነጋግሯቸዋል።ጋዜጠኛው አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ብሄራዊ ቡድኑን እንዲረከቡ ከታጩ አራት አሰልጣኞች አንዱ መሆናቸውን በመጥቀስ እድሉ በድጋሚ ቢሰጣቸው ቡድኑን ለመያዝ ምን ያህል ዝግጁ እንደሆኑ ላቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፤ «አሁን ይሄ ነው፤ይሄ ነው ብዬ በዝርዝር ለማለት ባልችልም፣ ሀገራዊ ኃላፊነት ሲሰጥህ መቀበል ግዴታ ነው። አንድ ወታደር የህይወት መስዋዕትነት እየከፈለ ግዴታውን እንደሚወጣ ሁሉ ሀገራዊ ግዴታ ከተሰጠኝ ለመቀበል ዝግጁ ነኝ፤ይህን ግዴታ በብቃት ለመወጣት ግን ምንም ዓይነት ቅሬታ የሌለበት ሙሉ ድጋፍ ማድረግን ይጠይቃል» ብለዋል።

እንግዲህ ይህን ያህል መንገድን የተጓዘ አሉባልታ ለማስተባበልም ይሁን አዎንታዊ ምላሽ ለመስጠት ፌዴሬሽኑ ለምን እንዳልፈለገ ለብዙዎች ግልፅ አይደለም። አሰልጣኙ ከተሰናበቱ ተሰናብተዋል፤ ካልተሰናበቱም «የሚወራው አሉባልታ መሰረት የለውም» ለማለት ፌዴሬሽኑን ለምን ከበደው።

በዚህ ጉዳይ ላይ መግለጫ ለመስጠት ጊዜ የሚፈጅ ጥናት ማድረግ አስፈላጊ ነው ተብሎ አይታመንም። ይልቁንም የፌዴሬሽኑ ዝምታ በስፖርት ቤተሰቡ ዘንድ የአሰልጣኙ መሰናበት እውን ሆኖ እንዲቆጠር ያደርጋል። ምክንያቱም አሰልጣኙ ከኃላፊነታቸው ካልተነሱ «አልተነሱም» ብሎ ማስተባበል ለምን አልተቻለም?። ስለ ሚወራው ነገር አልሰማንም ከሆነም ምላሻቸው «ሰምታች ኋል»እኛ ደግሞ ሰምታችኋል ነው የምንለው።

አሰልጣኙ ተሰናብተዋል ብለን እናስብ።ይህን ፌዴሬሽኑ ለህዝብ ይፋ ለምን ማድረግ እንዳልፈለገ መላ ምቶችን ማስቀመጥ እንችላለን። አንደኛ ፌዴሬሽኑ ረብጣ ዶላሮች እየተከፈላቸው ዋልያዎቹን ከስር ጀምሮ መሰረት ያስይዛሉ ተብለው የመጡት አሰልጣኝ አንዳችም ጠብ ያለ ነገር ሳያሳዩን እንዴት ተለቀቁ የሚለውን የስፖርት ቤተሰቡን ጥያቄ ፈርቷል። በሌላ በኩል የመገናኛ ብዙሃን ጫናን የፌዴሬሽኑ የሥራ ኃላፊዎች ለመጋፈጥ ድፍረት አጥተዋል።

ሁሉንም የሚያስማማው እየሆነ ያለውን ነገር ይፋ ማድረጉ ለፌዴሬሽኑ የሚያዋጣው መሆኑ ነው። አለበለዚያ እስከ መቼ ተደብቆ ይኖራል? በርካታ መገናኛ ብዙሃን ለህዝብ እርግጠኛውን መናገር አልቻሉም። « ህዝቡ እየጠየቀን ነው፤ ጥያቄያችንን መልሱ» ብለን እየጠበቅናችሁ ቀናት እያለፉ ነው። አሁንም የምንላችሁ ወይ ወስናችሁ ንገሩን፤ የሚመጣውን ጫና መሸከም ካቃታችሁ ደግሞ ኃላፊነቱን ለሚሸከም አስረክቡ።

እየተባለ ያለው እውነት ከሆነ አንድ ጥያቄ አንስቼ ሃሳቤን ልቋጭ። አሰልጣኝ ማርያኖ ባሬቶን ለመተካት የቀድሞው የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው፤ ውበቱ አባተ፤ ፀጋዬ ኪዳነ ማርያምና ዮሐንስ ሳህሌ ታጭተዋል ተብሏል። ቆይ እሺ ከእነዚህ አሰልጣኞች እኩል ልምድና ችሎታ ያላቸው እነ አሰልጣኝ አስራት ሃይሌና ስዩም ከበደስ?

ምንም እንኳ የቀድሞው አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ምክትል ስዩም ከበደ በየመን በክለብ ሥራ ላይ ቢገኝም ውሉን አቋርጦ ለመምጣት የሚከብደው አይመስለንም። ከራሱ እቅድ ውጭ የባለስልጣናት ጣልቃ ገብነትን አጥብቆ የሚቃወመው አስራት ኃይሌም ቢሆን አሁን በክለብ ሥራ የተጠመደ ባለመሆኑና የኢትዮጵያን እግር ኳስ ጠንቅቆ የሚያውቅ በመሆኑ ከእጩዎች ዝርዝር ውስጥ ሊካተት በተገባ ነበር።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ 

No comments:

Post a Comment