Thursday, February 12, 2015

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ በሱዳን ጉብኝት አደረጉ

(የካቲት 5/2007 , (አዲስ አበባ))--የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ በሱዳን ጉብኝት አደረጉ። በሱዳን ያለች ቤተ ክርስቲያን ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በየዓመቱ የ12ሺህ ዶላር ቦንድ እየገዛች ነው።

ብፁው ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ለአራት ቀናት ባደረጉት ጉብኝት ከአገሪቱ ባለሥልጣናትና የኢትዮጵያ ማህበረሰብ አባላት ጋር በጋራ ጉዳዮችና በልማት ላይ ተወያይተዋል። ፓትርያርኩ በቆይታቸው ከአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር አብደላ ሐማድ አልአዝራቅ በጋራ ጉዳዮች ላይ መክረዋል። ከሱዳን የሃይማኖት ጉዳይ ሚኒስትር አልፈታህ ታጅ ባደረጉት ውይይት ደግሞ ኢትዮጵያውያን በአገሪቱ እምነታቸው ተከብሮ ለሚያደርጉት እንቅስቃሴ አመስግነዋቸዋል።

ለዘመናት የኖረው የሃይማኖት መቻቻልና መከባበር ባህል አኩሪ መሆኑንም ገልጸዋል። ፓትርያርኩ በካርቱም ለከፍተኛ ክሊኒክና ለሊቃነ ጳጳሳት የተገነቡ ሁለት ሕንጻዎችን መርቀዋል።ለሌሎች ሁለት ሕንጻዎችም የመሠረት ድንጋይም አስቀምጠዋል። በሱዳን የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር አባዲ ዘሙ በበኩላቸው በአገሪቱ ያሉት ኢትዮጵያውያን አገራቸውን፣ባህላቸውንና ቋንቋቸውን እንዳይረሱ ለማድረግ በሚደረገው እንቅስቃሴ ቤተ ክርስቲያኗ ሚናዋን በመጫወት ላይ እንደምትገኝ አስታውቀዋል።

የፓትርያርኩ ጉብኝት በአገሮቹ መካከል ያለውን ግንኙነት የሕዝብ ለሕዝብ በማድረግም ድርሻ እንዳለው ተናግረዋል። በአገሪቱ ያለችው የደብረ ሰላም መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በየዓመቱ የ12ሺህ ዶላር ቦንድ ግዢ እያከናወነች መሆኗንም አምባሳደር አባዲ ገልጸዋል።

አቡነ ማትያስ ዛሬ ወደ አዲስ አበባ መመለሳቸውን የፓትርያርኩ ልዩ ጽህፈት ቤት ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት የላከው መግለጫ ያመለክታል።
ምንጭ:  ኢዜአ

Related topics:
ፓትሪያሪኩ ወደ ግብፅ ሄዱ  

No comments:

Post a Comment