Thursday, January 22, 2015

ዩኒቨርሲቲው ለቱርክ ፕሬዝዳንት የክብር ዶክትሬት ሰጠ

(ጥር 14/2007, (አዲስ አበባ ))--አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለቱርክ ፕሬዝዳንት ሬሲፕ ጣይብ ኤርዶጋን የክብር ዶክትሬት ሰጠ ፡፡ፕሬዚዳንት ኤርዶጋን የክብር ዶክትሬቱን ያገኙት በተለያዩ የአለም ክፍሎች ያሉ ለችግር ተጋላጭ የሆኑ ህዝቦች ፍትህና ዴሞክራሲን እንዲጎናፀፉ ከመደገፍ ባለፈ በአፍሪካ ላይ ያላቸውን አቋም መሰረት በማድረግ ነው።



የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶክተር አድማሱ ፀጋዬ እንዳሉት ፕሬዝዳንቱ  ሽብርተኝነትን በመታገል፣ ለበርካታ ስደተኞች የአገራቸውን በር በመክፈትና ሶማሊያን ጨምሮ የፈረሱ አገሮችን መልሶ በማቋቋም ረገድ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ በማበርከታቸው ነው፡፡

በቱርክና በኢትዮጵያ መካከል ያለው የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነት እንዲጠናከርም ሰርተዋል። የቱርክ ባለሃብቶች መዋዕለ ንዋያቸውን በኢትዮጵያ በማፍሰስ ለዜጎች የእውቀት ሽግግርና የስራ እድል እንዲፈጥሩ ፕሬዚዳንቱ አውንታዊ ሚና ተጫውተዋል።

ፕሬዝዳንት ኢርዶጋን በበኩላቸው በሁለቱ አገሮች መካከል ያለው ግንኙነት ከ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሩን አስታውሰው ባገኙት የክብር ዶክትሬት ዲግሪ መደሰታቸውን ገልፀዋል። ኢትዮጵያ በቀጣናው ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን እያደረገችው ያለውን አስተዋጽኦ ማድነቃቸውንና በሁለቱ አገሮች መካከል ያለውን ግንኙነት የበለጠ ለማሳደግ እንደሚሰሩም ተናግረዋል።

ፕሬዝዳንት ኢርዶጋን እንዳሉት የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱን ለማጎልበትም አገራቸው ለኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ነጻ የትምህት ዕድል መስጠቷን አጠናክራ ትቀጥላለች። ሁለቱ አገሮች በፖለቲካና በምጣኔ ሃብት ከመተባበር ባለፈ ሽብርተኝነትን በመከላከል ረገድም አብረው ይሰራሉ ብለዋል።

የኢትዮጵያ አቻቸው ፕሬዝዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ የእንኳን ደስ ያለዎት መልክታቸውን አስተላልፈዋል። "ትምህርት የአንድን አገር ሁለንተናዊ ጉዳይ የሚወስን ነው"ያሉት ፕሬዝዳንት ዶክተር ሙላቱ የአገሮቹን የትምህርት ተቋማት በማስተሳሰር ረገድ ፕሬዝዳንቱ ዩኒቨርሲቲውን መጎብኘታቸው ትርጉሙ የጎላ መሆኑን ተናግረዋል።

"ለአለም ህዝቦች ጥሩ አስተዋጽኦ ላበረከቱት የቱርክ ፕሬዝዳንት የክብር ዶክትሬት በመስጠቱ ዩኒቨርሲቲው ደስታ ይሰማዋል" ያሉት ደግሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ ሰብሳቢ አፈ-ጉባዔ ካሳ ተክለብርሃን ናቸው።

ኢትዮጵያ ድህነትን ለመዋጋት እየጣረች ባለችበት ወቅት ከአገሪቱ ጋር በትብብር እየሰሩ ላሉት ፕሬዝዳንት የክብር ዶክትሬት ለመስጠት ዩኒቨርሲቲው በአጭር ጊዜ ያደረገው ዝግጅትም የሚበረታታ ነው ብለዋል።

ዩኒቨርሲቲው ለፕሬዝዳንቱ የክብር ዶክትሬቱን የሰጠው አፍሪካን በመወከል እንደሆነም ተናግረዋል። በፕሮግራሙ ላይ የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት፣ አምባሳደሮች፣ የዩኒቨርሲቲው የቦርድ አመራሮች ተገኝተዋል።
ምንጭ:  ኢዜአ

No comments:

Post a Comment