Saturday, April 19, 2014

በዓሉ የመተባበርና የመደጋገፍ እንዲሆን የሃይማኖት አባቶች ጥሪ አቀረቡ

(Feb 18, 2014, (አዲስ አበባ))--ህዝበ ክርስቲያኑ የትንሳኤ በዓልን ሲያከብር ድጋፍ ለሚያሻቸው ወገኖች እገዛ በማድረግ ሊሆን እንደሚገባ የሃይማኖት አባቶች አሳሰቡ። የሃይማኖት አባቶቹ በዓሉን አስመልክተው ለክርስትና እምነት ተከታዮች የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።

የትንሳኤ በዓል ክርስቲያኖች አቅም ለሌላቸው ወገኖች የበለጠ የሚያስቡበት፣ በፍቅርና በርኅራኄም የተራቡትን፣ የተቸገሩትንና በስቃይ ላይ የሚገኙትን ወገኖች አቅም በፈቀደ የሚደግፉበት እንዲሆን አደራ ብለዋል።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ የትንሳኤ በዓልን ስናከብር የተራቡትን በማብላት፣ የተጠሙትን በማጠጣት፣ ጧሪ የሌላቸው አረጋዊያን፣ አሳዳጊ የሌላቸው ህፃናትንና የአካልና የአእምሮ ችግር የደረሰባቸው ወገኖችን በመደገፍ ሊሆን ይገባል ብለዋል፡፡

ህብረተሰቡ ለተፈጥሮ ልማት እያሳየ እንዳለው ትብብር ሁሉ ከስነ ምግባርና ባህል ያፈነገጡ ተግባራትን መከላከልንም የልማቱ አንድ አካል ማድረግ እንደሚኖርበት አሳስበዋል። ባለፉት ዘመናት በድህነትና ኋላቀርነት ስትሰቃይ የነበረችው ኢትዮጵያን በልማትና በእድገት ትንሳኤዋን ለማረጋገጥ ቃል መግባት እንደሚገባም ነው ያስገነዘቡት።

ለአገሪቱ እድገት የጀርባ አጥንት የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ሁሉም ዜጋ ድጋፉን አጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታልም ብለዋል። የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ብርሃነኢየሱስ ሱራፌል በበኩላቸው ምእመናን አቅማቸው በፈቀደው መጠን የተቸገሩ ወገኖችን በመደገፍ በአሉን በጋራ እንዲያከብሩ ጥሪ አቅርበዋል።

ለኢትዮጵያ ዕድገት ታላቅ ቦታ ያለውን የህዳሴ ግድብ ግንባታም ሆነ ሌሎችን የመሰረተ ልማት ስራዎች ከፍፃሜ ለማድረስ በሚደረገው ጥረት ህብረተሰቡ ከመንግስት ጎን መቆም እንደሚኖርበትም አሳስበዋል፡፡ የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተክርስቲያን መካነ ኢየሱስ ፕሬዚዳንት ቄስ ዶክተር ዋቅስዩም ኢዶሳም የትንሳኤ በዓል ሲከበር በሀገሪቱ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን በማጠናክርና ለታለመላቸው ግብ እንዲውሉ በማገዝ መሆን ይኖርበታል ብለዋል።

የህብረተሰቡ አካል የሆኑትን ወላጆቻቸውን ያጡ ህጻናትና ጧሪ የሌላቸው አረጋውያንን እግዚአብሔር ከሰጠን በማከፈል በዓሉን ማክበር ይገባናል ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል።  ሁሉም የሃይማኖት አባቶች በህመም ላይ የሚገኙ ወገኖችን፣ በማረሚያ ቤት ያሉ የህግ ታራሚዎችን፣ የአገርን ደህንነትን ለማስከበር በግዳጅ ላይ በአል ለሚያሳልፉ ወታደሮችና፣ በስራና በሌሎችም ምክንያቶች ከዘመድ ርቀው ለሚገኙ ሁሉ መልካም የትንሳኤ በዓል ተመኝተዋል።
ምንጭ፡ ኢሬቴድ 

No comments:

Post a Comment