Friday, April 18, 2014

ሕዝበ ክርስቲያን የትንሳኤን በዓል ሲያከብር ድሆችን መርዳትና መጠየቅ ይጠበቅበታል-ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

(Apr 18, 2014,  አዲስ አበባ))--ሕዝበ ክርስቲያን የትንሳኤን በዓል ሲያከብር ድሆችን፣ አጋዥ ያጡ አረጋውያንን በመርዳትና ድጋፍ በማድረግ ማክበር እንደሚገባ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስትያን አስታወቀች።

የቤተ-ክርስቲያኗ ፓትርያርክ ብጽእ ወቅዱስ አቡነ ማትያስን ጨምሮ በርካታ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንት ቤተ ክርስቲያን፣ ካህናትና ምዕመናን በተገኙበት ዛሬ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የፀሎት፣ የስግደትና የሕጽበተ እግር ሥርዓተ ኃይማኖት ተከናውኗል።

ብጽእ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት በዓሉ በሚከበርበት ወቅት ጧሪ ቀባሪ የሌላቸውን አረጋውያንን መርዳትና መደገፍ  ይገባል። ሕዝብ ክርስቲያንና መላ የኢትዮጵያ ሕዝብ የትንሳኤ በዓልን ሲያከብሩ የአገር ሠላም፣ ልማትና አንድነትን እያሰቡ ሊያከብሩ እንደሚገባ ነው የገለጹት።

ኃይማኖታዊ ሥርዓት መፈጸም የሚቻለው አገርና ሕዝብ ሠላማቸው ሲጠበቅ ነው ያሉት ብጽእነታቸው ልማት እንዲፋጠንና ብልጽግና እንዲረጋገጥ የሚያስችል መንገድ መወጠን ከሁሉም እንደሚጠበቅም አሳስበዋል። የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ አብርሃም በበኩላቸው ፀሎተ ሐሙስ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ሆኖ ሳለ የሐዋርያቱን እግር በማጠብ ትህትናን ያስተማረበት ዕለት ነው።

በመሆኑም ዕለቱ ጌታ በቤተ አልአዛር ተገኝቶ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን የሰጠበት ቀን የሚታሰብበት ዕለት መሆኑም አመልክተዋል። በመሆኑም ክርስቶስ ለሰው ልጆች እራሱን በሰጠበት ዕለት ሁሉም ሰው የተቸገረውን እንዲረዳ፣ የተራበውን እንዲያበላ የታመመውን እንዲጠይቅ የታሰረውንም እንዲጎበኝ ጥሪ አቅርበዋል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽህፈት ቤት የመንፈሳዊ ጉዳዮች ምክትል ሥራ አስኪያጅ ንብረ ኢድ ኤሊያስ አብረሃ በበኩላቸው አምላክ ከሰጠው ማዕድ ለተጠሙ፣ ለተራቡና ለታረዙ ማካፈል እንደሚገባ ተናግረዋል። ካለን ነገር አብረን ተካፍለን መብላትና መጠጣት፣ ወላጅ አልባ ሕፃናትን መደገፍና ረዳት የሌላቸውን ዜጎች ማገዝ እንደሚገባም ንብረ ኢድ ጥሪ አቅርበዋል።
ምንጭ፡ ኢሬቴድ 

No comments:

Post a Comment