Saturday, January 11, 2014

ሙያውን አዋርዶ ለማትረፍ መሯሯጥ ይበጃልን?

(Jan 11, 2014, (አዲስ አበባ))--የፕሬስ ነፃነት እንደ ሌሎች ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ሁሉ የአህጉራዊና ዓለም አቀፍ ተቋማትን ጨምሮ በዴሞክራሲያዊ ሀገራት ሕጎች ውስጥ ተቀባይነት ያለው የዜጎች/የሰዎች ዴሞክራሲያዊ መብት ነው፡፡ የፕሬስ ነፃነት ሃሳብን በጽሑፍና ሌሎች የሥነጥበብ ውጤቶች በነፃነት የመግለጽ መብት ነው። ለጋዜጠኞች ብቻ የተፈቀደ ልዩ መብትም አይደለም፣ የሁሉም ዜጎች መብት እንጂ፡፡ የፕሬስ ነፃነት የግልና የመንግሥት ጋዜጠኞችና ሚዲያ የሚል የልዩነት ወይም አድሎአዊ መስመር ያሰመረ አይደለም፡፡ በሀገራችን የፕሬስ ነፃነት ተገቢውን እውቅና ወይም ሕገመንግሥታዊ ዋስትና አግኝቶ በታሪካችን ተግባራዊ መሆን የጀመረው ከ1983 ዓ.ም ወዲህ ነው፡፡

ይህ የላቀ ዴሞክራሲያዊ መብት ወደ ተግባር ሲለወጥ ሚዛናዊና ተጨባጭ አድሎአዊነት የሌለው መሆን አለበት፡፡ የፕሬስ ነፃነት ሳንሱር ሳይደረግበትና ጫና ሳይኖረው በነፃነትና በሰላማዊ መንገድ ሃሳብን የመግለጽና አመለካከትን የማራመድ መብት ቢሆንም የሌላውን ግለሰብም ሆነ ቡድን መብት ወይንም ሃይማኖት፣ እምነትና አመለካከት እንዲድጥ፤ ማንነቱን፣ ክብሩንና ባህሉን እንዲያንቋሽሽ ወይም ለሽብር ተግባር፣ለግጭትና ሁከት መቀስቀሻነት እንዲውል የየትኛውም አገር ሕግ አይፈቅድም፡፡

የፕሬስ ነፃነት፤ ስሙን በመጠቀም ትርፍ ለመሳብ ብቻ ሲባል ከሙያው ሥነ ምግባር ባፈነገጠ መልኩ ጥላቻን ለማስረጽ የሚጠቀሙበት መብት አይደለም፡፡ የፕሬስ ነፃነት የመረጃ ምንጮችን ተአማኒነት፤ የሁለት ወገኖችንና የገለልተኛ ወገኖችን የተለያዩ ሃሳቦችና አመለካከቶች በእኩል ድርሻ የማንሸራሸር ኃላፊነትን ተግባራዊ ያደርጋል እንጂ አንድ ጥግ ይዞ በአንድ ወገን ላይ ብቻ የሚረባረብ፤ ጥላቻን የሚያመርትና የሚያዛምት አይደለም፡፡ ሀሰትን እውነት አድርጎ ማቅረብ፣ ለአንድ ወገን ተገዝቶ በሌላው ወገን ላይ መዝመት፤ መሰረታዊ የሃሳብና የአስተሳሰብ ልዩነቶች መከበር አለባቸው የሚለውን የዴሞክራሲ መሰረታዊ መርህ በመግደል የፕሮፖጋንዳ መሳሪያ መሆን የለበትም፡፡

የግለሰቦችን ስም ማጥፋት፤ ማጥላላት፤ ሰብዕናቸውንና ክብራቸውን ማጉደፍ ተአማኒነት የሌለው የፈጠራና የሀሰት ወሬ ማሰራጨት የፕሬስ ነፃነት ማለት አይደለም፡፡ አብሮነትን የሚያደፈርስ፤ ሕዝቡን ለሁከትና ለብጥብጥ ለትርምስ እንዲነሳ ከጀርባ የፋይናንስ ድጋፍ በሚያደርጉላቸው ኃይሎች እየተረዱ የሚዘወሩ መሆን የለባቸውም። ለሕዝብ የተሳሳተ መረጃን በማቅረብ እምነት እንዲያጣና ጥላቻ እንዲያደርበት በተሰላ መንገድ መቀስቀስ የፕሬስ ነፃነት ዓላማም ግብም አይደለም፡፡ የፕሬስ ነፃነት መብት የሕዝቦች ሙሉ መብት እንጂ ለጥቂቶች ብቻ ተለይቶ የተሰጠ ልዩ መብትም አይደለም፣ ሊሆንም አይችልም፡፡

የሕዝብን መብት ሰላምና ጸጥታ፤ እለታዊ ሕይወቱንና ኑሮውን፤ ማህበራዊ መስተጋብሩን የሚያናጉና የሚያደፈርሱ ጽሑፎችን እያተሙ ኃላፊነት በጎደለው መልኩ ማሰራጨት በዚህም የገበያ ትርፍ መሰብሰብ፣አልፎ ተርፎም ለሌሎች ስውር ፖለቲካዊ አጀንዳ ሽፋን ሰጪ፣ተላላኪና አገልጋይ ሆኖ መስራት የፕሬስ ነፃነት መርህ አለመሆኑን የዘነጉ አንዳንድ ፕሬሶች በሃገራችን ማቆጥቆጥ ከጀመሩ ሰነባብተዋል። በእርግጥ ይህ ትክክለኛው መንገድ ባለመሆኑ ጥቂት የማይባሉ የግል ፕሬሶች በራሳቸው ምክንያትና ጊዜ ዳር ሳይደርሱ ከመንገድ ቀርተዋል። አንዳንዶች ደግሞ ሙሉ ለሙሉ አሊያም ቢያንስ ከሞላ ጎደል ሕግና ሥርዓቱን ጠብቀው በመንቀሳቀሳቸው እስካሁንም ቀጥለዋል።

በሕዝብ ሚዲያው አካባቢም ጭልጥ ብሎ መደገፍና ሚዛናዊነት ማጣት የሚያዛልቅ አይሆንም። ስለሆነም መንግሥት ራሱም ለጉዳዩ ትኩረት መስጠት አለበት። በዋናነት ግን በውስጥና በይበልጥም በውጭ ባሉ ተቃዋሚ ኃይሎች/ጽንፈኞች የፋይናንስና የሞራል ድጋፍ እየተደጎሙ የእነሱ መሳሪያ በመሆን ለረጅም ጊዜ ሲያገለግሉ የነበሩ፤ በዚህም በርካሽ ጥቅም ራሳቸውን ያቃለሉና ያዋረዱ ምናልባትም በጣም ጥቂቶቹ በአጭር ጊዜ ሕይወታቸውን የቀየሩ፣ ሆኖም በፕሬስ ነፃነት ስም ሲነግዱ የነበሩና ዛሬም ያሉ ግለሰቦችን መታዘባችን አልቀረም።

መሰረታዊ ዓላማቸው፤ የፈጠራ ወሬ ነግዶ ማትረፍ እንጂ ለሕዝብና ለሀገር ጥቅም ወይም ብሔራዊ ክብር መቆርቆር አልነበረም፣ አይደለምም፡፡ ምንጊዜም ፍላጎታቸው ሕዝብንና ሀገርን ለችግር ዳርጎ በሕዝብ ሰቆቃ ማትረፍ፤ገንዘብ ማግበስበስ ሆኖ ሳለ «ለሕዝብና ለሀገር እንቆረቆራለን፤ መስዋዕትነት የምንከፍለው ለሀገርና ለሕዝብ ነው» ሲሉ መስማት ንጹህ ሕሊናን እያቆሰለ የምሬት ሳቅ ያስቃል፣ አዕምሮን ያደማል፡፡ ዳሩ ግን ሕሊናቸው እውነቱን ስለሚያውቀው በእዚህ ሥራቸው ሊያፍሩ እንጂ ሊመጻደቁና ሊኩራሩ ባልተገባቸው ነበር፡፡

በፕሬስ ነፃነት ስም በሚነግዱ ኃይሎች ስውር ተንኮል ተጠልፎ ነገር ግን ለሙያው ክብርና ነፃነት የሚሰራ መስሎት የሚታየው ጋዜጠኛ ካለ አንድ አፍታ ቆም ብሎ ራሱን በመጠየቅ ከሕሊናው መታረቅ ይገባዋል፡፡ በእርግጥ ለነማን ነው የምሰራው? ከጀርባ ማን ምን እያደረገ ነው? ብሎ መጠየቅ ግድ ይለዋል፡፡ ከትናንቶቹ ውድቀት መማርም ተገቢ ነው፡፡ በያዙኝ ልቀቁኝ ድንፋታና ኃላፊነትና ሙያዊ ሥነ ምግባር በጎደለው አካሄድ አንዳንድ የግል ፕሬሶች ከሕትመት ውጪ መሆን ከራሳቸው ሁኔታ ጋር በተያያዘ ምክንያትና አንዳንዶችም ከአቅም ማጣት ነው እንጂ በፕሬስ አፈና ምክንያት ተዘግተዋል የሚለው የፈጠራ ውንጀላ ፈጽሞ ተቀባይነት ሊኖረው አይችልም፡፡

ምክንያቱም የሀገሪቱ ሕገመንግሥት ለዜጎች ያጎናጸፈውን መብት ተጠቅሞና ሕግን ተከትሎ በሰላማዊ መንገድ የሚሰራን ፕሬስ ወይም ጋዜጠኛን መብት የትኛውም የመንግሥት አካል ሊጋፋ ወይም ይህን ሕገመንግሥታዊ መብቱን ሊነሳ የሚያስችለው ሕጋዊ መሰረት የለውም። ይህ ተፈጽሞ ቢገኝ እንኳ ማንም ዜጋ ቢሆን መብቱን በፍርድ ቤት ማስከበር የሚችልበት ሙሉ ነፃነት እንዳለው ይታወቃል።

በፕሬስ ነፃነት ስም የጽንፈኞች የፖለቲካ አጀንዳ ማራመጃ መድረክ የሆኑ አንዳንድ የግል ፕሬሶች ከስፖንሰሮቻቸው በተመደበላቸው ገንዘብ እንደሚንቀሳቀሱና በእነዚህ ኃይሎች ተጽዕኖ ሥር መውደቃቸው ይታወቃል። በግል ጋዜጠኝነት ካባ ተሸፍነው አሜሪካና አውሮፓ ላሉ የጽንፈኛ ተቃዋሚ ሚዲያዎች የሚሰሩ ወገኖች ስለመኖራቸው ከጥርጣሬም በላይ ነው። ይህ በሁለት ካባ (በሕጋዊና በሕገወጥ) ተሸፍኖ የሚሰራው ኃይል ነው እንዳሻው እየጻፈም እየዘለፈም፤ እየተቸም፤ እየተሳደበም፤ ኪሱን በመሙላት የፕሬስ ነፃነት የለም ሲል የሚደመጠው፡፡

 የፕሬስ ነፃነት ባይኖር ኖሮ ይህ ሁሉ የግል ጋዜጣና መጽሄት ለአደባባይ አይበቃም ነበር፡፡ ሊታረምና ሊስተካከል የሚገባው ችግር አለ ቢባል እንኳ በተጨባጭ ምክንያትና በሃቀኝነት ላይ ተመስርቶ ለሚመለከተው የመንግሥት አካል ማቅረብ፣ መንግሥትን መተቸት፣ ገንቢ አስተያየቶችንና መፍትሔዎችን ማመላከት አንድ ነገር ነው፡፡ ጭርሱንም የፕሬስ ነፃነት የለም ብሎ መደምደም ግን ጭፍን ክህደት ነው የሚሆነው፡፡ ከዚህ ይልቅ ያለውን ነፃነት ተጠቅሞ የራስን ብቃትና እውቀት እያሳደጉ መሄድ ጠቃሚ ነው። በተለይም መንግሥትን በተለያየ መልኩ በግልጽ የሚተቹ አስተያየቶችና አመለካከቶች ያለገደብ በነፃነት እየተስተናገዱ ባለበት ሁኔታ ውስጥ ሆነው ከሁለት አሥርት ዓመታት በፊት ሊሰማ ይችል የነበረና «ኧረ የፕሬስ ነፃነት ያለህ!» የሚያስብል፣ በባዶ ሜዳ ሙሾ የሚያስወርድ ነገር አሁን ምን አመጣው? ብሎ መጠየቅ ተገቢነት ያለው ይመስለኛል፡፡

እጅግ አስገራሚው ነጥብ ቀድሞ ከነበረው የተዛባ አስተሳሰብና አመለካከት በመነሳት ወይንም ስለፕሬስ ነፃነት በቂና ተገቢ የሆነ ግንዛቤና እውቀት ካለመጨበጥም የተነሳ አብዛኛው የግሉ ፕሬስ የፕሬስ ነጻነት መብት የእርሱና የእነርሱ የጥቂት ጋዜጦች መጽሔቶችና የግል ጋዜጠኞች ልዩና ብቸኛ መብት አድርጎ ይወስደዋል፣ ይህ አደገኛ ስህተት ነው፡፡ ማነው የፕሬስ ነፃነትን የግሉ ፕሬስ ብቸኛ መብት ያደረገው? የፕሬስ ነፃነት የዜጎች ሁሉ መብት ነው፡፡

በእርግጥ ከሙያው አንጻር በሕትመት ሚዲያው ዘርፍ ያሉ ጋዜጠኞች ብዙ ስለሚጽፉና ስለሚዘግቡ ሕግን ተላልፎ ከመገኘት የተነሳ ከሚያስከትለው ሕጋዊ ተጠያቂነት አንጻር ሊጠየቁ ስለሚችሉ የጻፍነው የፕሬስ ነፃነት መብታችንን ተጠቅመን ነው የሚለው የመከላከያ ምላሽ ሊሰማ ይችላል፡፡ ይህ ማለት ግን የግሉም ሆነ የመንግሥት ጋዜጠኛው ከሙያ ሥነ ምግባሩም ሆነ በብሄራዊና ዓለም አቀፋዊ የፕሬስ ነፃነት መርሆዎችና ሕጎች ላይ በግልጽ ከሰፈረው ውጪ ተራምዶ ቢሄድና ይህ ደግሞ የተለያዩ ችግሮችን በሕዝብና በሀገር ላይ የሚያመጣ ሆኖ ሲገኝ በሕግ አይጠየቅም፤ አይዳኝም፤ማለት አይደለም፡፡ እንዳሻው በልቅነትና በሕገ ወጥነት፤ በሥርዓተ አልበኛነት ሊፈነጭ ይችላል የሚል ሕግ የለም፡፡ ይህንን ዓይነት ሁኔታ የፕሬስ ነፃነት አሰፈንን የሚሉት እንግሊዝና አሜሪካንም በሕግ ከመዳኘት አላለፉም። እንዲያውም እንግሊዝ አዲስ ሕግ በፓርላማ እንዲወጣ እስከማድረግ ተረማምዳለች፡፡

ጽንፈኛና አክራሪ ፖለቲከኞች የሚጠቀሙበት አንዱ መንገድ ጋዜጦች ባሻቸው መንገድ ሕግ ተላልፈው እንዲጽፉ መገፋፋትና ጋዜጠኛው በሕግ ተጠያቂ ሲሆን ያንን በዓለም አቀፍ ድርጅቶች ማስተጋባት ነው። በዚህም በአገር ላይ ጫናዎችን ለመፍጠር የሚያደርጉት ጥረት ነው፣ ይህም የተቀናጀና የተጠና ሴራ ውጤት ነው፡፡ የፕሬስ ነፃነትን በመጠቀም የተለያዩ ጥቅሞቻቸውንና የፖለቲካ ዓላማቸውን ለማሳካት የሚንቀሳቀሱ የውጭ ኃይሎች በመሳሪያነት የሚጠቀሙት በዋናነት በሀገር ውስጥ ያለውን የግል ሚዲያ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በተደጋጋሚ በአፍሪካም ሆነ በእኛው ሀገር ውስጥ ታይቷል፡፡ ይህ ግን የት ድረስ ሊያዛልቅ እንደሚችል እንዳለፉት ጊዜያት ሁሉ በቀጣይም በተግባር መመልከቱ የሚበጅ ይሆናል። ፈቃደኝነቱና ዝግጁነቱ ካለ ካለፉ ስህተቶች መማርና ስህተትን ማረም በራሱ ትልቅ ነገር ነው።

የፕሬስ ነፃነት አንዱ የዴሞክራሲ መገለጫ እንደመሆኑ መጠን የተለያዩ የአስተሳሰብ ልዩነቶችንና የአመለካከት ጥጎችን ያከብራል፡፡ በእኩልነትም ያስተናግዳል እንጂ ከእኛ የተለየ አስተሳሰብና አመለካከት ያለው ሁሉ ጠላት ነው፤ አድርባይ ነው፤ የሚል የድንቁርና የጨለማ አስተሳሰብን ጭርሱንም አያስተናግድም፡፡ አይቀበልም፡፡ በእኛ አገር አንዳንድ የግል ፕሬሶች ይህንን መርህ ሲያከብሩ ሌሎች ደግሞ የዴሞክራሲንም ሆነ የፕሬስ ነፃነትን ምንነት ከቃል ውጪ በተግባር ስለማያውቁት ፍጹም ፀረ-ዴሞክራሲና ፀረ-ፕሬስ አቋም ያራምዳሉ፡፡

ለእነርሱ የፕሬስ ነፃነት ማለት ሀሜትና የመንደር አሉባልታን እውነት አስመስሎ ማቅረብ፤ ከሕግ በላይ የሆኑ እየመሰላቸውም ያሻቸውን ጽሑፍ እየጻፉ ጽንፈኞችን በመሳሪያነት ማገልገል፤ ሃሰተኛ ውንጀላ ይዞ መቅረብ ነው። በእነሱ የወረደ አስተሳሰብ ጀግንነትና ጋዜጠኝነት ነው ብለውም ያምናሉ፡፡ በሕዝቡ ስሜትና ችግር እየነገዱ ርዕስ እያስጮሁ ሆድ እያስባሱ በአቋራጭ የድህነት አቧራን በፕሬስ ነፃነት ስም ከላያቸው ላይ ያራገፉ ስለሚመስላቸው፤ ዛሬም በዚህ አቋማቸው የገፉበት ይመስላል፡፡ ለሀገር በሚጠቅምና በመረጃ ላይ የተመሰረተ ገንቢ ትችትና የማውጣጣት ሥራ ቢኖር እኮ ሁላችንንም በጠቀመን ነበር።

በአንዳንዶችም ዘንድ ይህንን ስር የሰደደ ችግር በለዘብተኝነት የመመልከት አዝማሚያ ይታያል፡፡ ምን ያመጣሉ የትስ ይደርሳሉ በሚል ግምትና አባባል ተገቢ መልስ ያለመስጠት ችግር ሕዝቡን የተምታታ ውዥንብርና ያለመረጋጋት ውስጥ እንደሚከተው ሥነ ልቡናውንም የማደፍረስ ጫና እንዳለው መመልከቱ ተገቢ ነው፡፡

ይህንን የላቀ ዴሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብት በተዛባ መንገድ እየተረጎሙት፤ ለጥፋት ድግስ ተላላኪ በመሆን በመሳሪያነትና በቅጥረኛነት የተሰለፉት ወገኖች፤ የሀገርንና የሕዝብን ታላቅነት፤ ሰላምና መረጋጋት፤ እድገትና ልማት፤ የሃሳብ ልዩነቶች ማክበርን፤ ተቻችሎናተከባብሮ፤ ልዩነትን ጠብቆ በሰላም መኖርን ደግመው ደጋግመው ሊያጠኑት ይገባል፡፡ ሰላምን ለማደፍረስ እየተራወጡ በውዥንብርና ግርግር ፈጠራ ነግጄ አተርፋለሁ፤ እከብራለሁ ብሎ ማሰብ የሕግና የሞራል ተጠያቂነት እንደሚያስከትል አስቀድሞ መገንዘብ ተገቢ ነው። ከሁሉም በላይ ግን ለሀገርና ወገን ጥቅምና ክብር መረጋገጥ በኃላፊነት ስሜት ሙያዊና የዜግነት ግዴታን መወጣት ላይ እናተኩር የሚለው መልዕክቴ ነው። 
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ 

No comments:

Post a Comment