Wednesday, November 06, 2013

የኤርትራ መንግሥት ፖለቲካዊ «ትራጀዲ»

(Nov 06, 2013, (አዲስ አበባ))--የዛሬን አያድርገውና መቀመጫው ኳታር ዶሀ ባደረገው «አልጀዚራ» ቴሌቪዥን ጣቢያ ስማቸው በመልካም ጐኑ እየተወሳ ለትዝብት በሚያጋልጥ ኢሚዛናዊ ዘገባ ይንቆለጳጰሱ ከነበሩ ጥቂት «የዓረቡ ዓለም አገራት መሪዎች ነን» ከሚሉት መካከል የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሣያስ አፈወርቂ አንዱ ናቸው፤ ወይም ነበሩ፡፡

ኤርትራ የአረቡ ዓለም አካል የሆነችው ከመቼ ወዲህ ነው የሚለው አወዛጋቢ ጥያቄ የማያወላዳ ምላሽ አለማግኘቱ ባይዘነጋም፣ ፈላጭ ቆራጩ ፕሬዚዳንት አቀላጥፈው በሚናገሩት የአረብኛ ቋንቋ ምክንያት ከዓለማችን ግዙፍ የሚዲያ ተቋማት ተርታ ለሚመደበው የአልጀዚራ ቴሌቪዥን ጋዜጠኞች ከወደ አፍሪካ ድንገት የተከሰቱ የአረብ ፖለቲከኛ ሳይመስሏቸው አልቀሩም፡፡

እናም በተደጋጋሚ ቀይ ባህርን ተሻግረው ወደ አሥመራ እያቀኑ የአዲሲቱን ምስራቅ አፍሪካዊት ሀገር «የነፃነት አባት» መጎብኘትና «በሕዝባቸው እጅግ የተወደዱ ታጋይ መሪ» ስለመሆናቸው የሚተርክ ዶክመንተሪ ፊልም ወይም ዘገባ በማጠናቀር የሰውዬውን አምባገነናዊነት የተጠናወተው ሰብዕና ፈፅሞ የማይገልፅ የፈጠራ ውዳሴ ከንቷቸውን እውነቱን የማወቅ ዕድል ለሌለው፣ የአልጀዚራ ቴሌቪዥን ተመልካች ሲግቱት ያስተዋልንበት ጊዜ ጥቂት እንዳልነበር ማስታወስ ተገቢ ይመስለኛል፡፡

የኢትዮ-ኤርትራ የድንበር ጦርነት ከተካሄደ በኋላ እንኳን፣ ፕሬዚዳንት ኢሣያስ አፈወርቂ «ከአንድ የሀገር መሪ በማይጠበቅ የተራ ሰው አለባበስና ነፃነት ያለምንም አጃቢ ሞተር ብስክሌታቸውን እየጋለቡ» ከአሥመራ ወደ ምፅዋ፤ ከምፅዋ ወደ አሥመራ ሲመላለሱ የሚያሳይ ውዳሴ ከንቱ ወይም አድናቆት የሚተረክበት ዘገባ በአልጀዚራ ቴሌቪዥን ሰፋ ያለ የሥርጭት ጊዜ ተሰጥቶት መተላለፉን መጥቀስ ይቻላል፡፡

«እውነትና ንጋት እያደር ይጠራል» እንዲሉ የኤርትራው ፕሬዚዳንት ሰብዕናም ሆነ የሚመሯት ሀገር ነባራዊ እውነታ፣ እነአልጀዚራ ሲተርኩልን ከኖሩት በተቃራኒ የመሆኑ ጉዳይ ፈፅሞ ሊስተባበል ወደማይችልበት ደረጃ ደርሷል፡፡ በኢሣያስ አፈወርቂ «ጦር አውርድ» የማለት አባዜ እየተቃኘ አካባቢውን ለማተራመስ ከመሞከር ቦዝኖ የማያውቀው የሻዕቢያ መንግሥት፣ «ትራጀዲያዊ ዘውግ» ባለው የፖለቲካ ተውኔቱ ኤርትራ ውስጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ የመጣውን ምጣኔ ሀብታዊ ቀውስ «በጐረቤት ኢትዮጵያ ባለሥልጣናት የሚሸረብ ሴራ» ያስከተለው ችግር እንደሆነ ለማስመሰል እንዲሁም የቀውሱን ሥፋትና ጥልቀት እያድበሰበሰ ለማቅረብ ያደረገው ከንቱ ጥረት ያቺ አገር «ሌላዋ ሶማሊያ» የመሆን ዕጣ እንደሚጠብቃት አሁን... አሁን ገሀድ እየወጣ የመጣውን ነባራዊ እውነታ በምንም ዓይነት ማስተባበል ከዓለም ኅብረተሰብ እይታ መሰወር አልተቻለም፡፡

ከዚህ የተነሳም አልጀዚራ የኤርትራ መንግሥት ያቺ አገር ነፃ ከወጣች ጀምሮ በኢሣያስ አፈወርቂ ፈላጭ ቆራጭ አመራር ሲተውነው የቆየውን «ትራጀዲያዊ» የፖለቲካ ተውኔት ለማጠቃለልና ያቺ «የአፍሪካ ሲንጋፖሪ» እንደምትሆን ፕሬዚዳንቷ በአንድ ወቅት የተመኙላት አገር ሌላዋ ሶማሊያ ወደ መሆን ልትቀየር በቋፍ ላይ እንደምትገኝ የሚያትት አሳዛኝ ዜና አሁን ይዘግብ ዘንድ ተገድዷል፡፡

«ኤርትራ ልክ እንደ ሶማሊያ መንግሥት አልባ አገር የመሆን ዕጣ ሊገጥማት ይችላል» በሚል ርዕስ ሰሞኑን አልጀዚራ ያሰራጨውን ዜና የዘገበው ጋዜጠኛ እንዲህ ዓይነት ድምዳሜ ላይ ለመድረስ ያስቻለበትን ወቅታዊ ምክንያቶች ሲያብራራም «የኤርትራው መንግሥት በእርግጥም እያለቀለት መሆኑን መረዳት የሚቻለው የባለሥልጣናቱ ኩብለላ እየተበራከተ የመምጣቱ ጉዳይ ነው...» ብሏል፡፡ ዜናው ሐተታውን ሲቀጥልም «በተለይም ደግሞ የፕሬዚዳንት ኢሣያስ ቀኝ እጅ የነበሩት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አሊ አብዶ መንግሥታቸውን ከድተው የፖለቲካ ጥገኝነት ለመጠየቅ መገደዳቸውን ስናጤነው ኤርትራ እንደ አገር የመቀጠሏ እድል ሳያከትም እንዳልቀረ ያመለክታል፡፡» ይልና ሌሎች ተያያዥ እውነታዎችንም ለዋቢነት ያህል በማውሳት ነው ሰሞነኛው የአልጀዚራ ዘገባ መራሩን ሀቅ ለመግለፅ የተገደደው፡፡

በቅርቡ አገራቸው የምትገኝበት አሳሳቢ ሁኔታ ያሰፈራቸው ኤርትራውያን አብራሪዎችም አንድ አውሮፕላን ይዘው ወደ ሣዑዲ ዓረቢያ መኮብለላቸውን ያስታወሰው ይኸው ሰሞነኛ የአልጀዚራ ወሬ የኢሣያስ መንግሥት የፓይለቶቹን መክዳት ካረጋገጠ በኋላ የወሰዷትን አውሮፕላን እንድታመጣ ወደዚያው የተላከችው ሌላዋ እንስት አብራሪም ሌላ ዜና አሰምታለች፡፡ እምነቱን ለጣለባት የአገሯ መንግሥት ታምና ሙያዊ ተልዕኮዋን በመፈፀም ፈንታ እንደቀደሙት ባልደረቦቿ እዚያው ሪያድ ለመቅረት መወሰኗን ጭምር ነው ዘገባው ያስረዳው፡፡ ለነገሩ ይህችው የሻዕቢያ መንግሥት «ታማኝ» አብራሪ በተለመደው የኤርትራውያን ዜጐች «አገራዊ ፍቅሪ» (የአገር ፍቅር ስሜት) ተገፋፍታ ለተሰጣት ሙያዊ ተልዕኮ ብትታመንና አውሮፕላኑን ይዛ ዳግም ወደ አሥመራ ብትመለስ ነበር የሚያስገርመው፡፡

የሰው ልጅ የመጀመሪያ ተልዕኮ ራስን በህይወት ማቆየት እንደ መሆኑ መጠን፣ ለጦረኛው ፕሬዚዳንት ኢሣያስ አፈወርቂ ልዩ ቀረቤታ የነበራቸው ኤርትራውያን ሳይቀር፣ ዛሬ ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ከሚወዷት አገራቸው ለመውጣት መገደዳቸው ተገቢና ሊደገፍ የሚገባው እንጂ የሻዕቢያ አጉል ጀብደኝነት የተጠናወተው ፖለቲካዊ ባህርይ ድምር ውጤት የሆነውን የዚያች አገር አሳዛኝ ፍፃሜ ከዚህ በላይ ይጋፈጡ ዘንድ አይጠበቅባቸውም፡፡

እንዲያውም የኤርትራ ሕዝብ «አገራዊ ነፃነት ለመቀዳጀት ሲባል» በተካሄደው እልህ አስጨራሽ የትጥቅ ትግል ወቅት የከፈለው ፈርጀ ብዙ መስዋዕትነት በሻዕቢያ መንግሥት የሥልጣን አያያዝ አለማወቅ ምክንያት መና እንዳይቀር ከማሰብ በመነጨ የኃላፊነት ስሜት፣ ሁኔታውን ሁሉ በመቋቋሙና የማይታመን ፅናት የሚጠይቅ ሆደ ሰፊነት ማሳየት በመቻሉ እንጂ እንደ ሥርዓቱ አስከፊነትማ ገና ድሮ ነበር ያቺ አገር ብትንትኗ የሚወጣው፡፡ ጉዳዩን በዚህ መልኩ ስናየው ሊያደርስ ከሚችለው ሞራላዊ ጉዳት አኳያ ተመልክተን ስንመረምረው ደግሞ የኢሣያስ ግፈኛ አገዛዝ በኤርትራ ሕዝብ ላይ ምን ያህል እንደቀለደና የፈፀመው ድርብርብ በደል ታሪክ ይቅር የሚለው እንዳልሆነ ይበልጥ ይገለፅልናል፡፡

እንግዲህ ኤርትራ «ነፃ አገር» ከሆነች ጀምሮ እንዳሻው ለመፍለጥና ለመቁረጥ የሚያስችለውን በትረ ሥልጣን ጨብጦ መላውን የአፍሪካ ቀንድ ቀጣና በጦረኛ ባህርይው ለማተረማመስና የፕሬዚዳንት ኢሣያስን የቁም ቅዥት ለማሳካት ሲሞክር የቆየው የኤርትራ መንግሥት በተከተለው የእብሪት መንገድ ምክንያት ከማንም በላይ ለፈርጀ ብዙ ጉዳት የተዳረገው ራሱ የኤርትራ ሕዝብ ስለመሆኑ ከሞላ ጐደል ለማመላከት ነው የእዚህ ጽሑፍ ዓላማም፡፡

ይህ ማለት ደግሞ በኢሣያስ አፈወርቂ የአጥፍቶ መጥፋት አመራር የሚተውነው የአሥመራ መንግሥት ፖለቲካዊ ትራጀዲ በሥልጣን ዘመኑ ሁሉ ያለአንዳች ተቀናቃኝ ያሻውን ለመፈፀም ያመቸው ዘንድ ገና «ኤርትራን ከኢትዮጵያ ቅኝ አገዛዝ ነፃ ለማውጣት» በሚል ሽፋን የተካሄደውን የትጥቅ ትግል ሲጀመር የዴሞክራሲ ያዊነት ባህርይ እንዳልነበረውና በተፈጥሮው አንስቶ ቅንጣት «ከእኔ ወዲያ ለአሳር ነው» የሚል አምባገነናዊነት የተጠናወተው ኃይል ስለሆነ እንጂ፣ የኤርትራ ሕዝብ እንዳሳየው ሆደ ሰፊነት ቢሆን ኖሮ ግን ያቺ አገር አሁን ወደምትገኝበት እጅግ ተስፋ አስቆራጭ ሁኔታ ባልተዘፈቀች ነበር እንደ ማለት ነው፡፡

ከእዚህ አጠቃላይ እውነታ ተነስተን የኤርትራን «ነፃ አገር» መሆን ተከትሎ፣ ሕዝቧ አንፃራዊ ሠላምና መረጋጋት እንዲያገኝ ከማድረግ ይልቅ በሻዕቢያው መንግሥት ማን አለብኝ ባይነት ምክንያት ከመላው ጐረቤቶቹ ጋር አላስፈላጊ ቅራኔ ውስጥ እየገባ የጎሪጥ እንዲተያይና ሁኔታው እየተባባሰ ሄዶም ኤርትራውያን ዜጐች ከነፃነት በፊት በሚያስገርም የዓላማ ፅናታቸው ከተጋፈጡት ዘርፈ ብዙ ፈተና ወደባሰ ማህበራዊ ቀውስ ለመግባት እንዲገደዱ በማድረግ ረገድ የኢሣያስ ግፈኛ ሥርዓት ለታሪካዊ ፍርድ ከመቅረብ እንደማያመልጥ እርግጠኛ መሆን ይቻላል፡፡

እንደተባለው «ኤርትራ ሌላኛዋ ሶማሊያ» የመሆን ዕጣ ገጠማትም በዚያች አገር ላይ ለደረሰውና ለሚደርሰው አሳዛኝ አወዳደቅ ሁሉ፣ ተጠያቂው ራሱ የኢሣያስ አፈወርቂ ግፈኛ አገዛዝ እንጂ ሌላ ምንም ሊሆን አይችልም፡፡ እንደእኔ እምነት ግን ኤርትራ ለይቶላት ልክ እንደ ሶማሊያ፣ መንግሥት አልባ ወደ መሆን ከማምራቷ በፊት፣ የሻዕቢያን ጦረኛ አገዛዝ እየተቃወሙ ስርዓቱን በመክዳት ላይ ያሉትን ለውጥ ፈላጊ ኤርትራውያን ጨምሮ፣ ሌሎቹም በዓለም ዙሪያ ተበትነው የሚኖሩት ሰላም ወዳድ የኤርትራ ዚጐች፣ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ተሰባስበው፣ ሀገራቸውን ከፍፁም ጥፋት የሚታደግ አንዳች የመፍትሔ ሃሳብ ማፈላለግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

በግልፅ አነጋገር የአሥመራው አምባገነናዊ ሥርዓት የሙጥኝ ብሎ የያዘው የጥፋት መንገድ በኤርትራ ሕዝብ ህልውና ላይ የጋረጠውን አስፈሪ አደጋ ከወዲሁ ለመቀልበስና ያቺም አገር ልክ እንደቀድሞ የሶማሊያ ሪፐብሊክ ጥቂት የጦር አበጋዞች ጎራ ለይተው በሚፈጥሩት የሥልጣን ሽኩቻ ምክንያት ብትንትኗ ወጥቶ ሌላ የዓለም አቀፋዊ የሥርዓት አልበኝነት መፈንጫ (የሽብርተኝነት መናኸሪያ) እንዳትሆን ለማድረግ ይቻል ዘንድ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ በጋራ መክረው ዘክረው ፍቱን መላ መምታት ይኖርባቸዋል፡፡

ምንም እንኳን የማንኛውም ሉዓላዊ አገር ሕዝብ ለየራሱ ውስጣዊ ችግር ዘላቂ መፍትሔ በማፈላለግ ረገድ ቀዳሚውን ሚና ይጫወት ዘንድ ግድ ቢሆንም ቅሉ ኤርትራውያን ወገኖቻችን ዛሬ ያሉበትን አሳሳቢ ቀውስ ስናጤነው የዚያቺ አገር ሕዝብ ከመቼውም ጊዜ በላይ ውጫዊ ድጋፍ እንደሚሻ የሚያጠያይቅ አይደለም፡፡ ከዚህ አኳያም ጉዳዩ በአንድ ወይም በሌላ መልኩ የሚመለከታቸው የምሥራቅ አፍሪካ አገራት በአባልነት የተካተቱበት «ኢጋድ» እንዲሁም የአፍሪካ ህብረት ኤርትራ ውስጥ አሁን እየሆነ ያለውን የከፋ ሁኔታ በተመለከተ ተገቢ ትኩረት ሰጥተው ከመከታተል ሊቦዝኑ አይገባም የሚል እምነት በብዙዎች ዘንድ አለ፡፡ 
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment