Monday, June 03, 2013

የኢትዮጵያና ግብጽ ጠቅላይ ሚኒስትሮች ተወያዩ

(ግንቦት 26/ 2005, (አዲስ አበባ))--በጃፓን እየተካሄደ ባለው አምስተኛው የቶክዮ ዓለም አቀፍ የአፍሪካ ልማት ጉባኤ ላይ እየተሳተፉ የሚገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያም ከግብፅ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀሻም ቃንዲል ጋር ተወያይተዋል ።

በውይይታቸው ላይም በዋናነት ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አብይ አጀንዳ ሆኗል ። ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያም ግድቡ ግብፅ የምታገኘውን የውሃ ድርሻ እንደማይጎዳው ለቃንዲል አረጋግጠውላቸዋል።

በሌላ በኩል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ቴዎድሮስ አድሃኖምና የጃፓኑ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ፉሚዮ ኪሺዳ የአገሮቻቸውን ግንኙነት አስመልክቶ ከትናንት በስቲያ ውይይት አድርገዋል። በውይይቱ ወቅት የጃፓኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢትዮጵያ በጉባኤው ላደረገችው ተሳትፎና ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ጉባኤውን በተባባሪነት በመምራታቸው ምስጋና ማቅረባቸውን መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል።

ፋሚዮ ኪሺዳ እንደተናገሩት፤ ጃፓን በቶኪዮ ዓለምአቀፍ ለአፍሪካ ልማት መድረክ አማካኝነት ወደፊትም ለአፍሪካ የምታደርገውን ድጋፍ አጠናክራ ትቀጥላለች። ዶክተር ቴዎድሮስ በበኩላቸው፤ በአፍሪካና በጃፓን መካካል ጠንካራ ወዳጅነት ቢኖርም በኢኮኖሚው ዘርፍ ግን በትብብር ከመስራት አኳያ ብዙ እንደሚቀር ገልጸዋል፡፡

ጃፓን እንደሌሎች የኤስያ አገራት ሁሉ በአፍሪካ ኢንቨስት ማድረግ ለሚፈልጉ ባለሃ ብቶቿ ድጋፍ እንድታደርግም ዶክተር ቴዎድሮስ በእዚሁ ወቅት ለጃፓኑ አቻቸው ጥሪያቸውን አቅርበዋል ፡፡ የወንዙን ፍሰት ማስቀየስ በውሃው መጠን ላይ ተፅእኖ አይኖረውም አዲስ አበባ፤ የአባይ ወንዝ ተፈጥሮአዊ ፍሰት መቀየር በታችኛው ተፋሰስ ሃገራት ላይ ምንም አይነት ጉዳት እንደማያስከትል የኢት ዮጵያ ኤሌክትሪክ ሃይል ኮርፖሬሽን ገለጸ፡፡

የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ምህረት ደበበ እንደተናገሩት፤ ግድቡ የሚገነባው በወንዙ መካከል ላይ በመሆኑ የወንዙ አቅጣጫ መቀየሩ በታችኛው ተፋሰስ ሃገራት ላይ ተጽእኖ አለው የሚሉ ወገኖች ምንም መነሻ የላቸውም። ከእዚህ በፊትም በተመሳሳይ በአገሪቱ በተገነቡት ግድቦች ላይ «የወንዝ ማስቀየር ስራ ተከናውኖ በውሃ ፍሰት መጠን ምንም አይነት ተፅእኖ አልነበረውም» ያሉት አቶ ምህረት፤ አሁንም በአባይ ወንዝ ላይ የተከናወነው የፍሰት ማስቀየስ ተግባር ሙሉ ለሙሉ ፍሰቱን እንደጠበቀ እንደሚያስኬደው ተናግረዋል።

በአሁኑ ወቅት በዓለም ላይ የሚገነቡ ትልልቅ የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድቦች በተመሳሳይ መንገድ የወንዝ ማስቀየስ ስራ እንደሚከናወንባቸው ጠቁመው፤ በዓባይ ወንዝ ላይ የሚገነባው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታም የታችኛው ተፋሰስ ሃገራትን በማይጎዳ መልኩ በጥናት ላይ ተመስርቶ እየተከናወነ መሆኑን መግለጻቸውን የኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቭዥን ዘግቧል።

መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ. ም ግንባታው የተጀመረው የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ሲጠናቀቅ ስድስት ሺ ሜጋዋት ያመነጫል ተብሎ ይጠበቃል።
ምንጭ አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment