Monday, February 18, 2013

ፓትሪያርክ ለመምረጥ በምዕመናንና ካህናት ሲካሄድ የቆየው ጥቆማ ተጠናቀቀ

(Feb 18, 2013, አዲስ አበባ)--6ኛውን የኢትዮጵያ ፓትሪያርክ ለመምረጥ ከየካቲት 1 እስከ 8 በምዕመናንና ካህናት ሲካሄድ የነበረው ጥቆማ መጠናቀቁን የቤተክርስቲያኗ  አስመራጭ ኮሚቴ አስታወቀ፡፡

በምዕመናኑና በካህናቱ የተካሄደው የእጩ ፓትሪያርክ ጥቆማ በሚመረጡ ከ3 እስከ 5 እጩዎችን በመያዝ አስመራጭ ኮሚቴው ከተወያየ በኋላም የካቲት 16 ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ያቀርባል፡፡

የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስና የአስመራጭ ኮሚቴው ሰብሳቢ ብጹእ አቡነ እስጢፋኖስ እንዳሉት 6ኛውን የፓትርያርክ ምርጫ ጥቆማ በአካልና በፋክስ በሺዎች የሚቆጠሩ ካህናትና ምእመናን ሲሳተፉ ቆይተዋል፡፡

አስመራጭ ኮሚቴውና ቅዱስ ሲኖዶስ ከ3 እስከ 5 በተመረጡ እጩዎች ላይ ከተወያዩ በኋላ የካቲት 18 ቀን ይፋ እንደሚደረግ ብጹእ አቡነእስጢፋኖስ ተናግረዋል፡፡ የካቲት 21 ቀን በሚደረገው 6ተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የፓትርያርክ ምርጫ ከሀገሪቱ አብያተ ክርስቲያናትና ከአለም አብያተ ክርስቲያን ምክር ቤት የተውጣጡ ምእመናንና ካህናት  በታዛቢነት ይሳተፋሉ ብለዋል፡፡

የምርጫው ሂደት በሰላም እስኪጠናቀቅም የቤተ ክርስቲያኒቱ  ሊቃነጳጳሳት ፣ ካህናትና ምእመናን ጸሎት እንዲያርጉ ብፁእ አቡነ እስጢፋኖስ ጥሪ አቀርበዋል፡፡

No comments:

Post a Comment