Wednesday, September 26, 2012

የደመራ በዓል ዛሬ ተከበረ

(አዲስ አበባ መስከረም 16/2005)--የደመራ በዓል አዲስ አበባ ውስጥ በደማቅ ሥነ-ሥርዓት ዛሬ ተከበረ፡፡ በበዓሉ ላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስትያን ዓቃቢ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ብጹእ አቡነ ናትናኤል መስቀል የሠላም ምልክት መሆኑን ገልጸው ምእመናን በሠላምና በፍቅር እንዲሁም በመቻቻል በጋራ ድህነትን ሊዋጉ ይገባል ብለዋል፡፡ 



የእምነቱ ተከታዮች በተለይም ወጣቶች ኃይማኖታዊ በዓላትን ከማክበር ጎን ለጎን የተጀመሩትን የልማት ሥራዎች ለመፈፀም በጋራ እንዲሰሩ አባታዊ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡ በዓሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዳክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስትን እና ብሔራዊ በዓል ቢሆንም ከዚህ ቀደም በተባበሩት መንግሥታት የባህልና የትምህርት ድርጅት /ዩኒስኮ/ ዕውቅና ተሰጥቶት በዓለም ቅርስነት እንዲመዘገብ የተጀመረው ጥረት እንዲቀጥል ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

የአዲስ አበባ አስተዳደር ከንቲባ ተወካይ አቶ ፀጋዬ ኃይለማሪያም በበኩላቸው በዓሉን ብሔር ብሔረሰቦች ከጥንት ጀምሮ ያከብሩት እንደነበር አስታውሰው በዚህ በዓል ላይ የሚታየውን አንድነት በፀረ-ድህነት ትግሉም ላይ ተጠናክሮ እንዲቀጥ ጠይቀዋል፡፡ የኃይማኖት ተቋማትም ተከባብረው መንግሥት የዘረጋውን የፀረ-ድህነት ስትራቴጂና የአምስት ዓመቱን የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ለማስፈፀም ከመንግሥት ጎን ሊቆሙ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡ 

በበዓሉ የአዲስ አበባ ከተማና በከተማዋ ዙሪያ የሚገኙ ገዳማትና አድባራት ሊቃውንትና የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ዝማሬና ወረብ ያቀረቡ ሲሆን የፌዴራል ፖሊስ ማርሽ ባንድም በዓሉን አስመልክቶ መንፈሳዊ ዝማሬዎችን አሰምቷል፡፡ 

ደመራውን ሊቀጳጳስ ብጹእ አቡነ ናትናኤልና የከንቲባ ተወካይ አቶ ጸጋዬ ኃይለማሪያም በጋራ ለኩሰዋል፡፡ በመስቀል አደባባይ በተከበረው በዚህ በዓል ላይ ጥንድ ድርብ የለበሱ መዘምራንና ልብሰ ተክህኖ የለበሱ ካሕናት እንዲሁም በአገር ባህል ልብስ የተዋቡ ምእምናንና በርካታ የውጭ አገር ጎብኝዎችና ዲፕሎማቶች ተገኝተዋል፡፡ 
Source: ENA

No comments:

Post a Comment