Sunday, November 27, 2011

የኑሮ ውድነት ፈታኝ የአዲስ አበባ ችግር መሆኑን አስተዳደሩ አስታወቀ

(23 Nov 2011, Reporter)--"ዛሬም ከኪራይ ሰብሳቢነት አረንቋ አልወጣንም›› ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ" በዓለም የኢኮኖሚ ቀውስና በንግድና ግብይት ሥርዓት ቅልጥፍና ማነስ ምክንያት በአዲስ አበባ የተከሰተው የኑሮ ውድነት ችግር፣ ፈታኝ ከሚባሉ የከተማዋ ችግሮች መካከል አንዱ መሆኑን ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ አስታወቁ፡፡

ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ ትናንት ለተወካዮች ምክር ቤት አባላት ባቀረቡት አጭር መግለጫ እንዳስታወቁት፣ የአቅም ግንባታና የመልካም አስተዳደር እጦት አሁንም ከባድ ፈተና ሆኖ የተጋረጠባት አዲስ አበባ፣ የኑሮ ውድነቱም የራሱን ተፅዕኖ እያሳረፈ የሚገኝባት ከተማ ሆናለች፡፡

አስተዳደሩ ሥልጣኑን ሲረከብ በዓለም ደረጃ ተከስቶ የነበረው የእህል የዋጋ ንረት ቀውስ በአገሪቱና በከተማዋ ላይ ጥላውን በማጥላት ከባድ ፈተና ሆኖ እንደነበር ያስታወሱት ከንቲባው፣ ችግሩን ለማስወገድ ከፌዴራል መንግሥትና ከሕዝቡ ጋር በመቀናጀት ጥረት ቢደረግም፣ ችግሩ አሁንም ልዩ ትኩረትን የሚሻ ፈተና መሆኑ በግልጽ መታየቱን አስታውቀዋል፡፡

የአዲስ አበባ ቁልፍ ችግር ነው ተብሎ ሌላው በአስተዳደሩ የተጠቀሰው ጉዳይ የኪራይ ሰብሳቢነት አደጋ ነው፡፡ አዲስ አበባ የኪራይ ሰብሳቢነት የበላይነት ሰፍኖ የሚገኝባት ከተማ በመሆኗ፣ በዋነኞቹ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች ላይ የተጀመሩትን የለውጥ ዕርምጃዎች በከፍተኛ ደረጃ እየተፈታተናቸው እንደሚገኝ አቶ ኩማ በሪፖርታቸው ገልጸዋል፡፡

‹‹በተለይ በመሬትና በግብር ጉዳዮች ላይ አትኩረን ኪራይ ሰብሳቢነትን ለማስወገድ ሰፊ ጥረት ስናደርግ ብንቆይም፣ ሠራን ባልንባቸው በእነዚህ መስኮችም ቢሆን ዛሬም ከኪራይ ሰብሳቢነት አረንቋ አልወጣንም፤›› ብለዋል፡፡
Source: Reporter

No comments:

Post a Comment